Saturday, March 22, 2014

ነብዩ ሲራክ በመልካም ሁኔታ ላይ መሆኑ ታወቀ

(EMF) ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ከማህበራዊ ድረ ገጾች የጠፋው፣ የጅዳው ጋዜጠኛ ነብዩ ሲራክ በሳዑዲ ፖሊሶች ተይዞ ባልታወቀ እስር ቤት ውስጥ መታሰሩ ተገልጾ ነበር:: ሆኖም ዛሬ ከሳኡዲ አረብያ ያገኘነው መረጃ እንደሚያስረዳው ከሆነ፣ ነብዩ ሲራክ የግል እረፍት ላይ መሆኑ ተገልጿል:: በሌላ አገላለጽ “ነብዩ ሲራክ አልታሰረም!” ነብዩ በተለይ በሳኡዲ አረብያ የሚገኙ ኢትዮጵያዊ ወገኖች ይደርስባቸው የነበረውን ሰቆቃ ከስፍራው በመዘገብ እና ሁኔታውን ለህዝብ ሲያሳውቅ እንደነበር ይታወሳል:: ከዚያም በተጨማሪ ለጀርመን ሬድዮ ጣቢያም ከጅዳ ቃል አቀባይ ሆኖ ሲሰራ ነበር::
Bebiyu Sirak
Bebiyu Sirak
በቅርቡ የመታሰሩ ዜና በሰፊው መሰራጨት የጀመረው በጅዳ የኢትዮጵያ ቆንስላ ጽ/ቤት ሰዎች አማካኝነት መሆኑን መረጃዎች ያመለክታሉ:: እነዚሁ ለገዢው መንግስት አገልጋይ የሆኑት የቆንስላው ሰራተኞች “ነብዩ ከመጠጥ እና ሴት ጋር በተያያዘ በሳዑዲ ፖሊሶች ቁጥጥር ስር ውሏል” የሚል ወሬ እንዳናፈሱበት እና ይህንኑ ተከትሎ መልካም ስሙን ለማጥፋት የበኩላቸውን ጥረት ማድረጋቸውን መረጃዎች ያመለክታሉ::
Nebiyu Sirak
Nebiyu Sirak
ነብዩ ሲራክ በሳኡዲ በኢትዮጵያውያን ላይ ይደርሱ የነበሩ ግፍ እና በደሎችን ያለመታከት ሲዘግብ ነበር:: በዚህም ምክንያት ለነዚህ ወገኖች ለመድረስ በተቋቋመው የሳኡዲ ኮሚቴ ውስጥ አባል ሆኖ ሲሰራ ቆይቷል:: ሆኖም ከግዜ በኋላ በቆንስላ ጽ/ቤቱ የሚፈጸመውን በደል ጭምር ማጋለጥ በመጀመሩ በነዚህ ሰዎች ዘንድ በአይነ ቁራኛ ሲጠበቅ ነበር:: በመካከላቸውም አለመግባባት ከተፈጠረ ቆየ:: ይህን አስመልክቶ የሆነውን በራሱ ብዕር እንዲህ ገልጾ ነበር:: እኛም ነብዩ ሲራክ በመልካም ሁኔታ ላይ የሚገኝ መሆኑን የደረሰን ዘገባን መሰረት አድርገን የዘገብነውን ዜና እዚህ ላይ አብቅተናል:: የነብዩ ሲራክን የመጨረሻ መልእክት እንድታነቡት በመጋበዝ እንለያችኋለን::
ቀዩ ካርድ ! ወገን ለወገን ደራሽ ኮሚቴ ዛሬ ምሽት “የዲሲፕሊን !” እርምጃ ወሰደ !
እኔም መረጃ ማቀበሌ ወንጀል ሆነና ከኮሚቴው ታገድኩ !
በርካቶች ሪያድ መንፉሃ አይናችን ጉድ ሲያይ ችግሩ ወደ ጅዳ እንዳይዛመት ሰጋን ። እናም እንደ ጋዜጠኛ ብቻ ሳይሆን ዜጋ የዜጎች ጉዳይ ያገባናል የምንል ዜጎች ልናደርግ በምንችለው ድጋፍ ዙሪያ መከርን ። በነጻ ግልጋሎት ዜጎችን ለመርዳት በሚል ለጅዳ ቆንስል ጥያቄ አቀረብን። ጥያቄውን ለማቅረብ የተወከልነው በቀጣይ በተደረገው ስብሰባ ተመርጥን ። እንዲያ ሆኖ በጊዜያው መረዳጃ ኮሚቴ ውስጥ በጸሃፊነት ተመርጨ እስከ ዛሬዋ ቀን አገለገልኩ ። በቆይታየ ወቅት በዜጎች ፣ መብት ጥበቃ ፣ መረጋጋት ፣ ብሎም ነዋሪውና በሳውዲ መንግስት እና በዲፕሎማቶች መካከል ያለውን የመረጃ ልውውጥ በማንሸራሸር ብሎም ለዜጎች ድጋፍ ለማመላከት የተሰየሙ በርካታ ስብሰባዎችን ተካፍያለሁ። ከስብሰባ ወጥቸ በሰፊው ነዋሪውን በምደርስባቸው ማህበራዊ መገናኛ መስመሮች ዜጎቻችን ወደ ሃገር ግቡ በሚለውን መልዕክት በተገቢ መንገድ ለማስተላለፍ ሙከራ ሳደርግ ፈታኝ ጥያቄዎች ይቀርቡልኛል። እኒህን በነዋሪው የሚነሱ አንኳር አንኳር ጥያቄ እና አስተያየቶች በጠረጴዛ ዙሪያ ከማቅረብ ባለፈ በግል ከሃላፊዎች በኩል መልስ ለማግኘት ብሞክርም አልሳካልህ አለኝ !
ባሳለፍነው ሳምንት ስምምነት ጠፍቶ ግብ ግብ እስከ መግጠም ስናዘነብል እኔም ነገሩ አላምርህ ብሎኝ ከኮሚቴው ለመሰናበት ጥያቄ አቀረብኩ! ይህ በሆነበት ምሽት ዲፕሎማቶችን ጨምሮ በኮሚቴው አባላት ሽምግልና ሃሳቤን እንዳጥፍ ግድ አለኝ ። እንዲህ ስንጓዝ ስልክ ወደ ሚመለከታቸው የቆንስል ሃላፊዎች ደውሎ የማረጋጋቱንም ስራም ሆነ እንደ ኮሚቴ መረጃ መቀባበል የማይታሰብ እየሆነ መጣ …የነዋሪው ምሬት ደግሞ ያንኑ ያህል እያደግ መጣ!በኮሚቴው በኩል ቢያንስ ቆንስል መስሪያ ቤቱ ስብሰባ ጠርቶ ህዝቡ ይመከር የሚለው ወደ መፍትሄ ለማምጣት የምናደርገው ሙከራ ተደጋግሞ ቢጠየቅም በቆንስላው ሃላፊዎች ተቀባይነት ማጣት ደጋግሞ ተኮላሸ፣ ከሸፈ! ይህ በመሆኑ የወገኖቸን ሮሮ በካባቢው ያለውን መረጃ በግል የማድረስ የለመድኩትን መረጃ ቅበላ ተያያዝኩት!
እነሆ ይህ አካሔዴ ያላማራቸው የገዠው የፖለቲካ ድርጅት አባላት በዚያ አረንጓዴ ቢጫ ቀይ ባንዴራችን በተሰቀለበት ቤታችን ብቸኛ ተጽዕኖ ፈጣሪዎች ናቸውና በኮሚቴው ላይ ጫና ሲያሳርፉ ሰንብተው እነሆ ዛሬ ተሳካ! ማግለያው “ዲሲፕሊን እርምጃ! ” የሚል ስም ተለጠፈበት … ቀዩ ካርድ ዛሬ አመሻሽ ላይ ተመዘዘ! ከኮሚቴው አባልነት ተወገድኩ! ለእኔ የተመዘዘው ካርድ “በቆንስሉ ፖስፖርት ለማደስ ስመጣ በአንድ አስተናባሪ ተደፈርኩ!” ላለችውም ሆነ ወደ ሃገር የሚሸኙ ግፉአን ዜጎችን እቃ በመጫን ሲያጭበረብሩ በተያዙት የፖለቲካ ድርጅት አባላት ላይ በቂ ማጣራት ተደርጎ ፍትህን ያገኛሉ ብየ ልሰብ … ቢያንስ ካልተድበሰበስ ጉዳዩ ከተጣራና ከተረጋገጠ እነርሱ እንደኔ “የዲሲፕሊን ” ሳይሆን ወንጀል ፈጽመዋልና ከድርጊታቸው ማስተማሪየሰ ቢሆን ቀዩ ካርድ ሊሰጣቸው ይገባል! ይህ የእኔ ምኞት ነው …! በመጨረሻ ይህችን ልብል …በቆይታየ መረጃ በማቀበል ትብብር ስታደርጉልኝ ለቆያችሁ ሁሉ ምስጋና ማቅረብ እወዳለሁ! አመሰግናለሁ! አዎ! “ዲሲፕሊን! ” ያሉትን ውሳኔውን በጸጋ ተቀብያለሁ … ይህም መረጃ ነውና ወዳጆቸ ማወቅ አለባችሁ ብየ ስለማምን ላሳውቃችሁ ግድ አለኝ ! ከሁሉም በላይ የወገን ሮሮ ሊታፈን ፣ ሊዳፈን አይገባም! በደል እስካለ ሮሮ አለ! ሮሮ ካለ መረጃ ቅበላውን በቀይ ካርድ ሆነ በተለያየ ማጥቂያ ዘዴ ማስቆም ከቶውን አይቻልም! ዘመኑ የመረጃ ነው! እኔም የመስማት የማየት መረጃ የማቀበል መብት ፣ ዜጋውም መረጃ የማግኘት የማይገሰስ መብት አለው!
ሰላም
ነቢዩ ሲራክ
ይድረስ ከደማም ለምትገኙ ኢትዮጵያውያን

No comments:

Post a Comment