Thursday, March 13, 2014

በሕገወጥ ተግባር የተሰማራ ኤምባሲ፡ ካርቱም (አብርሃ ደስታ)


በዓለም ዉድድር አለ። ዉድድሩ በህዝቦች መካከል ነው። ህዝቦች ዉድድሩን ለማሸነፍ አብሮነትን ይፈልጋሉ። በአብሮነት የራሳቸው ደህንነትና ጥቅም ማስከበር ይሻሉ። ደህንነታቸውንና ጥቅማቸው ለማስከበር ሀገር ይመሰርታሉ። ሀገር መስርተው በመንግስት ይወከላሉ። የመንግስት ተግባር ታድያ የህዝቡን ጥቅምና ደህንነት መጠበቅ ነው። በዚሁ መሰረት መንግስት የህዝቦች ተወካይ ጠበቃ መሆን ይጠበቅበታል።
Abraha Desta the facebook
አብረሃ ደስታ
የህዝቦች ወኪል (ጠበቃ) ለመሆን መንግስት በተለያዩ ሀገሮች ኤምባሲ ይከፍታል። የኤምባሲው ሰራተኞች የሚወክሉትን ህዝብ ጥቅምና ደህንነት ይጠብቃሉ፣ ያስጠብቃሉ። ለዚሁ ተግባራቸው ሲባል ህዝብ ደሞዛቸውን ይከፍላቸዋል። ደሞዛቸው የሚከፈላቸው ከመንግስት ካዝና ነው። የመንግስት ገንዘብ የሚሰበሰበው ከህዝብ ነው፤ በግብር መልክ።
የኢትዮጵያ መንግስትም (መንግስት ልበለው) ከህዝብ ኪስ የሚከፈሉ የኤምባሲ ሰራተኞች አሉት። በተለያዩ ሀገሮች ያሉ የኢትዮጵያ ኤምባሲ ሰራተኞች በህዝብ ገንዘብ እየተዳደሩ የሚከፍላቸውን ህዝብ የሚበድሉ መሆናቸው እናውቃለን። ዛሬ ትኩረቴ የሳበ ግን በካርቱም ያለው የኢትዮጵያ ኤምባሲ ነው።
ካርቱም የሚገኙ ጓደኞቼ እንደላኩልኝ ከሆነ የኢትዮጵያ ኤምባሲ (በካርቱም) ሰራተኞች በሕገወጥ የሰዎች ዝውውር ተግባር ተሰማርተው ኢትዮጵያውያንን አደጋ ዉስጥ እየጣሉ ይገኛሉ። የሰዎች ደህንነት ከመጠበቅ ይልቅ ሰዎችን አደጋ ዉስጥ ማስገባት ምን ይሉታል? የመንግስት አካላት ወንጀልን ከመከላከል ይልቅ ቁማርተኞች ሲሆኑ ምን ማድረግ ይቻላል?!
የኢትዮጵያ ኤምባሲ ሰራተኞች ሱዳን ዉስጥ የሚቸገሩ ዜጎቻችንን ደህንነት ከመከታተል ይልቅ ከሱዳን መንግስት ጋር በመተባበር ኢትዮጵያውያን እስርቤት ይከታሉ። እስካሁን ድረስ በሱዳን ብዙ ኢትዮጵያውያን ያለ ምንም ጠያቂ በወህኒቤቶች እየማቀቁ ነው። የኢትዮጵያ ኤምባሲ ሰራተኞች በሱዳን ሀገር የሚደርስባቸው ችግር፣ እስር፣ እንግልት እያወቁ በሰዎች ንግድ መሰማራታቸው ይገርማል። የኤምባሲው ሰራተኞች በሀገራቸው ሰዎች ንግድ ነው የተሰማሩ።
በሱዳን ያሉ ኢትዮጵያውያን መንግስት እንደሌላቸው (መንግስት አልባ እንደሆኑ) ነው የሚቆጠረው። “ሑዳ” በሚባል ወህኒቤት 35 ጠያቂ የሌላቸው ኢትዮጵያውያን አሉ። እነዚህ እስረኞች ያለ ምንም የፍርድቤት ዉሳኔ የተያዙና ከ8-12 ዓመት በወህኒቤቱ የቆዩ ናቸው። ተሰቅለው የተገደሉም መዓት ናቸው። በሱዳን የኢትዮጵያውያን ህይወት ርካሽ ነው። መስከረም አያሌው የተባለችም በሰባት ሱዳናውያን መደፈሯ ይታወሳል።
ኢትዮጵያውያን መንግስት አልባ (stateless) ሁነው ሲሰቃዩ የኤምባሲው ሰራተኞች ግን ሰዎች እየገዙና እየሸጡ (በሰዎች ንግድ ተሰማርተው) ገንዘብ ይሰበስባሉ። ዘመናዊ መንግስታዊ የንግድ ባርያ መሆኑ ነው።
ኢትዮጵያውያን ክብራችንን የምናስመልስበት ግዜ ሩቅ አይሆንም። አቶ መሐመድ ቱፋና አቶ በላቸው ግን ተግባራቹሁ ሁሉ እየተከታተልነው እንገኛለን።
It is so!!!

ትዝብት – ደርሶ መልስ ዲያስፖራ (አንደኛ)


አትክልት አሰፋ (ቫንኩቨር)
ነገሩ የሆነው አዋሳ ዩኒቨርሲቲ ነው። ቆነጃጅት ወጣት ሴት ተማሪዎች ከዩኒቨርሲቲው ቅጥር ግቢ ውጭ ባሉ የከተማው ደለላዎች ጋር በመተባበር እጅግ ዘግናኝ ስራ ይሰራሉ። ደላሎቹ የቆነጃጅቶቹን ተማሪዎች ፎቶ የያዘ ትልቅ ካታሎግ ይዘው ከአዲስ አበባም ሆነ ከአቅራቢያው ከተሞች አለዚያም ከዚያው ከአዋሳ ከተማ ብቅ የሚሉ ሃብታም ደንበኞቻቸውን የተማሪ ኮረዶችን ፎቶ በመስጠት ያስመርጣሉ።
ሰውየው ውብ ወጣት ተማሪ ኮረዳ እንደሚፈልግ በሰው በሰው የተገናኘውን ደላላ ይጠይቃል። እናም ከተሰጠው የፎቶ ድርድር ላይ ማመን ያቃተውን የአንዷን ውብ ፎቶ እያሳየ ‘ይህችን ታውቃታለህ?’ ሲል ይጠይቃል። የደላላ መልስ አንድ ነው… ሁሉንም ስለሚያውቃቸው አልተቸገረም ‘አዎ እሷን ይፈልጋሉ?’ ሲል ይጠይቃል። ሰውየውም ‘እባክህ’ ሲል በመማጸን ፈቃደኝነቱን ይገልጻል። ከፊቱ የመጣለትን ገቢ ተደራድሮ ልጅትን ለመጥራት ይሮጣል። ደላላው።
እናም ቆንጅት ተበጃጅታ፣ አምራና ደምቃ ትመጣለች። በቀጥታ ወደ ሰውየው መኪና ስትደርስ ሰውነቷ ይርዳል። በቁጣ አይኑ የተንቀለቀለው ሰውየም ወደ ልጅቷ ያፈጣል… በቀጥታ ተንደርድሮ የልጅቷን ክርን ይይዛል… ደላላው እየሆነ ያለውን ሊረዳ አልቻለም… የልጅቷን እጅ የያዘው ሰው (ደንበኛ) የልጅቷ ወላጅ አባት ኖሯል።
ኢትዮጵያ ደርሶ የሚመጣ የውጭ ሀገር ነዋሪ (ደርሶ መልስ ዲያስፖራ) በተለያየ አይነት እይታ የተለያዩ እውነታዎችን ይዞላችሁ ይመጣል።
አንዳንዱ የህንጻውን ግንባታ አዳንቆ ሲያወራ፤ ሌላው ስለጭፈራ ቤቶች ይዘክራል። ጓደኞቹን በስራ ብዛት ሊያገኝ እንዳልቻለ የሚያወራላችሁ እንደመኖሩ ሁሉ በስራ አጥነት ችግር የተነሳ ዱርየ መበራከቱን የሚተርክላችሁ አታጡም። የቆነጃጅቶችን ውበትና የዳንኪራ ቤቶችን ሁናቴ የሚነግራችሁ፤ በየቡና ቤቱ ብሎም በየትምህርት ቤቱ ያሉ ወጣቶችን ችግር ያስረዳችኋል። የሀገሪቱን እድገት በኮንስትራክሽን መጥለቅለቅ የሚያጫውታችሁ፤ በመንገዱን መቆፋፈር ሰው ስለመማረሩ በማንሳት ያትትላችኋል። አዲስ አበባን በመመስረት ላይ እንዳለች ታላቅ ከተማ አድርጎ የሚተርክም አታጡም።
ይሄ ሁሉ እንደ እድገት በአንዲት መንግስት የሚባል አካል አላት በተባለች ሀገር መታየቱ ምኑ ይገርማል?። አንዳንዴ ሀገሩን አይቶ ዘመድ ወዳጅ ጠይቆ መምጣትም ሆነ ሰው ሀገሩ ደርሶ መመለሱ እጅግ መልካም ነገር ነው። ያየውን ግልብ ነገር ከራሱ አይን ጥግ ስር አንጻር ብቻ ተመልክቶ በሰዎች ላይ የሚደርስን ስቆቃ ሸፋፍኖ ያለጥናት የተሰሩ መንገዶችንና ህንጻዎችን እንደትልቅ ለውጥ ማውራት ግን የሞራል ጥያቄን ያመጣል።
በእርግጥ የውብ ሀገር ነችና ውቦች ሊኖሩ ይችላሉ። መሸታ ቤቶቹም ደማምቀው ሊሆን ይችላል። ህንጻ ግምባታውም ቢጧጧፍ አያስነውርም። መንገዶች ተንጣለው ቢታዮም ጸጸት የሚገባው የለም። ነገር ግን ሰው በቀላሉ ቆሎ ሽጦ ይኖርበት ከነበረ መንደር ተባሮ መግቢያ ያጣበት ሀገር፤ ውሃ ልማት የቆፈረውንና ውሃ ቧንቧ ቀብሮ ያበጀውን መንገድ ነገ ቴሌ የሚያፈርሰው ከሆነ… ከዚያም ማዘጋጃ ቦይ ተደፈነ ብሎ ከተረተረው… ወጣት እንስት ህጻን ታናሽ እህቷንና ወንድሟን ትምህርት ቤት ለመስደድ መንገድ ከወጣች፤ ጥቂት የባለጊዜ ልጆች የሚሰሩት አጥተው በተንፈላሰሱባት ሀገር መለመንን ተጠይፈው ዱሮ የነበራቸውን ጽዱ ልብስ ለብሰው ፊታቸውን የከለሉ ሰዎች በየጥጋጥጉ የሚለምኑባት ሀገር ከሆነች… አባት ትምህርት ቤት ብሎ የላካት ወጣት በኮሌጅ ያለውን ፍላጎቷን ለማሳካት ገበያ መውጣት… ዘግናኝ ነው…
የሚሰራው መንገድ ተሸርሽሮ ከአመት በላይ አገልግሎቱ አልቆለት ተቦርቡሮና ውሃ ቋጥሮ የሚታይበት ሀገር እየገነቡ መሰረት መጣል አይቻልም ነው ጥያቄው። ደረጃቸውን ባልጠበቁና በይድረስ ይድረስ የተሰሩ ህንጻዎች ጋጋታ የከተማንም የሀገርንም እድገት ሊያሳዩ አይችሉም ነው እየተጮኸበት ያለው ነገር። ፍትህ ራሷን ችላ የምትራመድበትን ሀገር የሚመራ መንግስት ይኑር ነው ልፈፋው። የህወሃት ሰዎችና ጥቂት አሸርጋጆች የሚያደርጉት አገራዊ ጥፋት ይቁም። ልጆቻችን እርስበርስ የዚህና የዚያ ብሄር ወይንም ከወዲያ አለዚያም ከወዲህ መንደር የመጡ እየተባባሉ በጥርጣሬ እየተያዩ የሚኖሩበትንና የሚያድጉበትን ሀገር እናፈራርስ ነው እሪታው። የህወሀት አለያም ጥቂት ሽርጉደኞች በገፍ የሚገነቧቸው ህንጻዎች ከሙስና ባሻገር ሆኖ ራሳቸው ኢንጂኒዬርና አርክቴክት ሆነው የሚገነቡት ሀገር ሀገር አይሆንም ነው ጉዳዩ።
22 አካባቢ የተሰራው ጎላጎል ህንጻ ባለጊዜው ባለቤት ህንጻውን ሲያስገነባ ዋናው መንገድ ውስጥ መግባቱን ያየ መሀንዲስ ወይንም ኢንጂኒዬር ‘አግባብ አይደለም፤ ወደፊት መንገድ ይዘጋል’ ብሎ ምክር ቢሰጠው ‘እኔ ያልኩህን አድርግ’ ብሎ ጀርባውን የተማመነው ባለቤት ሲያዘውና ያ ባለሙያ የታዘዘውን በማድረጉ ግንባታው ከተጠናቀቀ በኋለ አሁን መንገዱን የዘጋውን ህንጻ የሚደፍረው ጠፍቶ፤ መረማመጃው ዘግቶ መታየቱ የሚወራው ዝም ብሎ ከመሬት ተነስቶ አይደለም።
አሁንማ የህወሃት ሰዎች እጅግ ከመድፈራቸው የተነሳ አዲስ አበባ ውስጥ በስማቸው ሆኗል ፎቅ የሚያስገነቡት ተክላይ ህንጻ፣ ገብረጻዲቅ ህንጻ… ብሎ ያጫወተኝ ወዳጄ ታዲያ ምን ችግር አለው? ስለው ‘ምንም ችግር የለውም በህዝቡ ውስጥ ግን የማህበራዊ ህይወት መራራቅንና ሃሜትል ያስከትላል ብሎም ህዝቡን እነሱ እና እኛ የሚያስብል የሳይኮሎጅ ጣጣ ውስጥ ከቶታል።” አለኝ
ሀገሪቱን የህወሃት ጄኔራሎችና መኮንኖች ብቻ በሀብት የወረሯት ሀገር ተሸክሞ የት እንደሚደረስ ማሰብ ሰው መሆን ነው። ይህ ወዳጄ ታዲያ በአንጻሩ የሽንኩርትን ገበያ ለማየት ጉሊት ወርዶ ያየውን ጉድ በልኩ አስተውሎ መጥቷል። አንድና ሁለት ራስ ትንንሽ ሽንኩርት አልያም ቲማቲም ለሳምንት ለማብቃቃት የሚሰቃይ ህዝብን ይዞ ጉዞው የት ነው የሚያደርሰን።
የአገሪቱን የዘር ችግር ጥግ ላይ መድረስ ባለፈው 767 አውሮፕላንን ይዞ ጄኔቫ የገባው ወጣት ረዳት አብራሪን በሚመለከት መግለጫ የሰጡት ሬድዋን ሁሴን “ጠላፊው ከየት ነው?’ ተብለው ሲጠየቁ ‘ኢትዮጵያዊ ነው’ ብለው ሲመልሱ አረ ከየትኛው ክልል ተብለው መጠየቃቸው ጉድጓድ ውስጥ የሚከት ቅሌት ነው። መልሳቸውም እረሪሪሪሪሪ የሚያስብል ነበር። ‘ከየትኛው ብሔር እንደሆነ አልታወቀም።’
መጠጥና ዳንኪራ ቤቶች
ከ5 ሚሊየን ህዝብ በላይ (እስከ 8 ሚሊዮን ይገመታል) የሚኖርባት አዲስ አበባ የጭፈራ ቤቶችን ብዛትና የጨፋሪውን አይነት የነገረኝ ወዳጄን ቀኑን ሙሉ ሲተራመስ የሚውለው አዲሳቤ በጊዜ በ12 ሰዓት ከቶ በየፊናው ሲገባ ከተማው ምን ያህል ጭር እንደሚል አላስተዋለም። 100 የማይበልጡ ምሽት ቤቶች (አጋንኘው ነው) 100 ሰው እያንዳንዳቸው ቢያገኙና ቢያስጨፍሩ 10ሺህ ሰው… እንጨምረው እና 50ሺህ ሰው በምሽት ስለጨፈረና ስለደነከረ ሀገር በጥጋብ እንደዘለለ ማውራት ነውር ነው ነው ጨዋታው። ይሄንኑ ግምት እናስላው ከተባለ የገዥው ህወሃት/ኢህአዴግ ባለስልጣናትና ጥቅም ተሻራኪዎች 70 በመቶውን ቢያነሱ 15 በመቶ በዲያስፖራና ዘመዶች እንዲሁም የተቀረው ለፍቶ አዳሪ አለያም ከቤተሰቡ የሚቃርም ሊሆን ይችላል።
ለነገሩማ የዘመነኞቹ ሰዎች ልጆች የሚገቡበት ቡና ቤት ውስጥ ቀድሞ የገባ ሌላ ደንበኛ ሾልኮ እንዲወጣ የሚደረግባት ምድር። በድርድር የታሰረ ብር ለአስተናጋጅ ተሰጥቶ ቆጥረሽ ውሰጅ የሚል ረብጣው ያጨናነቀው የዘመኑን ሰው ማየት የተለመደ መሆኑንም እየሰማን ነው።
ምን እዚህ እኛ በብርድ እየወጣን ሰላማዊ ሰልፍ እያልን እንጮሃለን እነሱ ሚሊየነሮች ሆነዋል ያለኝና ሀገር ቤት ሄዶ በጓደኛው የቀና ሰው ያጫወተኝም አለ። ያ ጓደኛው ከዘመንኛ ሰዎች ጋር ገጥሞ ህዝብ እየቦጠቦጠ መሆኑን የነገረኝ ደርሶ መልስ ዲያስፖራ… አሁንም እዚህ ኖርዝ አሜሪካ ከተመለሰ በኋላ እዚያው አገር ቤት ቢሆን እንደጓደኛው ሚሊየነር ይሆን እንደነበር ሲያወጋኝ በመቆጨት ነበር። ዘመንኞቹና ጓደኛው የሚቦጠቡጠው ህዝብ ስቃይ በሚሊየን ብር ተጋርዶበት። አረ እየተስተዋለ! እዚያኮ ሀገር እየተቆራረሰ ነው! አረ ስለአምላክ! ሀገሪቱም በመንደር እየተተበተበችኮ ነው! ስለእመብርሃን! ምድራችን ፍትህ የጠፋባት ሆናለችኮ! በሽብርተኛ ስም ስንቱ ታጎረ… አረ ስለአላህ! ሰው ኑሮ መረረኝ እያለ ነው እኮ! እንኳን ከአሜሪካ ከመንግስተ ሰማያትም አመጣኻለሁ የሚል ለስራው ብቁ ያልሆነ ሰው የሚሾምበት ሀገር ውስጥ የሚኖር ህዝብ እኮ ነው የያዝነው። ጭራሽ የሶማሌ ክልል ባለስልጣን ይባስ ብሎ ምኒባስ ታክሲ በከተማ እንዳይገባ ብሎ በራሱ ስልጣን አግዶ እገዳውን የጃፓን መንግስት ቢመጣም እንኳን አልቀበልም እያለ እኮ ነው ጎበዝ… ሰሚ የለም እንዴ በግዜር!?
ለዛሬ ላብቃ!
ቸር ለእናንተ!!!