Saturday, March 16, 2013

ስኬታማ አገር አቀፍ ተቃውሞ… ዛሬም ድምጻችንን አሰምተናል!

                                                                                                                                         March 16,2013
ድምፃችን ይሰማ
ሻሸመኔ በውጥረት ውላለች!
ደሴዎች በሙሉ ኃይል ተመልሰዋል!
ስኬታማ አገር አቀፍ ተቃውሞ… ዛሬም ድምጻችንን አሰምተናል!ትግላችን ከተሞችን እያዳረሰ ነው! የዛሬው ‹‹ድምጻችን ይሰማ በሁሉም ከተማ›› ተቃውሞ ከተጠበቀው በላይ በሆነ ስኬት ተጠናቋል! በአገራችን በሁሉም አቅጣጫ የሚገኙት ከተሞች የተባበረ እና በትግል የተዋሐደ የፍትህ ጥሪያቸውን አሰምተዋል።
ባለፈው ሳምንታት ሲካሄድ እንደነበረው የዛሬው ተቃውሟችንም በሶስት እርከን የተከፈለ መሆኑ ይታወሳል። በመጀመሪያውና በአንድ ማእከላዊ መስጊድ ተሰባስቦ በመስገድ የትግል አጋርነትን የማሳየት ተቃውሞ በየከተሞቹ በታሰበላቸው መስጊድ በድምቀት ተካሂዶ ውሏል። መሳጂዶቹ ለወትሮው ከሚሰግድባቸው ሰው ላቅ ያለ ሰጋጅ አስተናግደውም ውለዋል። የመቀሌው አንዋር መስጊድ እና በአፋር ከተሞች የሚገኙ መሳጂዶች ላይ የተስተዋለው የሰው ብዛት አመርቂ የነበረ ሲሆን በአፋር መሳጂዶች ደማቅ የቁኑት ዱአ ስነ ስርአትም እንደተካሄደባቸው ተጠቁሟል። የባህር ዳር ሙስሊሞችም በበኩላቸው አላህ የመጣውን ፈተና እንዲያነሳ የዱአ ስነ ስርአት ጭምር አካሂደዋል።
በአንዳንድ ከተሞች ወረቀት የመበተኑ ስራ ተሟሙቆ ውሎ ነበር። በወልቂጤ ከተማ ብቻ ከሱብሂ ሰላት በኋላ ከ20 ሺህ በላይ ስለትግሉ የሚያስገነዝብ በራሪ ወረቀት ተበትኗል። በአዲስ አበባ የአንዋር መስጊዱ ተቃውሞ ዛሬ አንዋርን ባዶ በማድረግ የተቀየረ መሆኑን ተከትሎ ለወትሮው ቁጣቸውን በሚገልጹ አስር ሺዎች ውስጡና ዙሪያው የሚሞላው ታላቁ አንዋር መስጊድ ዛሬ በአስገራሚ ሁኔታ ባዶውን የዋለ ሲሆን እጅግ ጥቂት ሰዎች ብቻ ሰግደውበታል። በተለዋጩ ፒያሳ የሚገኘው ኑር መስጊድ እና በመርካቶው ባዩሽ እንዲሁም በሾላው ሱመያ መስጊዶች እጅግ በርካታ ሙስሊሞች የጁምአ ሰላታቸውን አከናውነዋል፡፡ ብዙዎች ህዝበ ሙስሊሙ እያሳየ ያለውን ቆራጥነት እና ታዛዥነት ያሳየበት አጋጣሚ ስለመሆኑ አስተያየታቸውን ሰጥተዋል። በዛሬው የአዲስ አበባ ተቃውሞ አንድ አንድ ሰዎች እንደተገነዘቡት መስጊዶን ቦይኮት የማድረግ ሳይሆን ተቃውሞችንን በተለያዩ መንገዶች መግለጽ እንደምንችልና በዚሁም አንደነታችንን እና ታዛዥነታችንን ከፍ አድርጎ ለማሳየት ነበር፡፡ በዚያውም አንዋር ተቃውሞ ሲኖር የሚመጣውን ሕዝብ ተቃውሞ ከማይኖርበት ወቅት ጋር አነጻጽሮ የህዝቡን ብዛት ልዩነት ለተመልካች ጭምር ማሳየትም ነበር፡፡
በሁለተኛ እርከንነት የተያዘው የዝምታና የምልክት ተቃውሞ በበኩሉ በበርካታ ከተሞች ላይ ሲካሄድ እንደዋለ ተዘግቧል። በተደጋጋሚ የመንግስት ሀይሎች ድብደባና ጥቃት ልትበገር ባልቻለችው ደሴ ከተማ ሙስሊሙ ህብረተሰብ በሜጠሮ ሸህ ጁሐር መስጊድ በከፍተኛ ቁጥር ተሰባስቦ ጁምአን ከሰገደ በኋላ እጆቹን በማያያዝ፣ በማቆላለፍ እና የተለያዩ ምልክቶችን በማሳየት ተቃውሞውን አሳይቷል። የሺዎች እምባ ጉንጮችን በሚያርስበት የዱአ ፕሮግራምም በችግር ውስጥ ላለው ሙስሊም ህብረተሰብ መሪር ዱአ አድርጎ በሰላም ተበትኗል። በዚያው ክልል ኮምቦልቻ ከተማ በሚገኘው ኻሊድ መስጊድ በርካታ ሙስሊሞች ተሰባስበው የዝምታ ተቃውሞ አካሂደዋል። የአህባሽ መጅሊስ ጭብጡን አጥብቆባታል በምትባለው በዚህች ከተማ ይህን መሰል ተቃውሞ በመታየቱም በርካቶች ደስታቸውን ገልጻዋል። ተቃውሞው የተጠናቀቀው በዱአ ነበር።
በተመሳሳይ ወቅት ደቡብ በምትገኘው ደማቋ የንግድ ከተማ ወራቤ ከፍተኛ ቁጥር ያለው ሙስሊም ማህበረሰብ በአቡበክር መስጂድ ተሰባስቦ የዝምታ ተቃውሞውን በማካሄድ ለኢትዮጵያውያን ሙስሊሞች ታላቅ ትግል ያለውን አጋርነት አረጋግጧል። በድሬዳዋ ከተማ ሳላህ ደብአን መስጂድ ኢማሙ ለህዝበ ሙስሊሙ እና በግፍ ለታሰሩ ጀግኖቹ አላህ መፍትሄውን እንዲያመጣ ዱአ ያደረጉ ሲሆን አሸዋ ሰፈር በሚገኘው ቢላል መስጊድም የቁኑት ዱአ ስነ ስርአት መደረጉ ተዘግቧል።
በሶስተኛው የተቃውሞ እርከን ውስጥ ያሉት ቀሪዎቹ ከተሞች በበኩላቸው በሻሸመኔ እና አዳማ ከተፈጠረው የጸጥታ ችግር በስተቀር ስኬታማና የደመቀ ጁምአ አሳልፈው ውለዋል። ዛሬ ለሁለተኛ ጊዜ ተቃውሞዋን ባሰማችው ዲላ ከተማ አስተዳደሩ ተቃውሞ እንዳይኖር ከፍተኛ ጥረትና ማስፈራሪያ ያደረገ ቢሆንም ሳይሳካለት ቀርቷል። የዲላ ጀግኖች በመስጂዳቸው ከቀሪ ኢትዮጵያውያን ወንድሞቻቸው የተለየ ድምጽ እንደሌላቸው አሳይተዋል። በርካታ መፈክሮችንም አሰምተዋል። በመቱ ከተማ ነጃሺ መስጊድ እንደ እስከዛሬው ሁሉ በርካታ ሙስሊሞች ድምጻቸውን ያሰሙ ሲሆን ‹‹የሀገራችንን ሰላም እያደፈረሰ ያለው የሀይማኖት አክራሪነት ሳይሆን የፖለቲካ አክራሪነት ነው›› የሚል ጽሁፍ ከፍ አድርገው በማሳየትም ተቃውሞ አሰምተዋል። በተቃውሞው የሴቶች ተሳትፎ ጎልቶ የወጣ የነበረ መሆኑ ታይቷል።
በአላባ ከተማ ኑር መስጊድም እንዲሁ ከ20 ደቂቃዎች በላይ የዘለቀ ከፍተኛ ተቃውሞ ተደርጎ ውሏል። ከጁምአ በፊት አንድ የአካባቢው አንጋፋ አሊም ለህዝበ ሙስሊሙ ዱአ ማስደረጋቸውም ተገልጾዋል። በድምጽ ተቃውሞው መሀል የመስጂዱ ኢማም ተቃውሞውን ለማስቆም ሙከራ አድርገው የነበረ ቢሆንም የአላባ ሙስሊሞች ግን ውስጣቸው የታመቀውን ብሶት ከመግለጽ አልተቆጠቡም። ተከታታይና ደማቅ ተቃውሞዎችን ስታስተናግድ የሰነበተችው ዶዶላ ከተማና አካባቢዋም የፍትህ ጥሪ ስታሰማ ውላለች። በከተማይቱ በፈትህና ሙጅመእ መሳጂዶች ላይ ከፍተኛ የድምጽ ተቃውሞ የተደረገ ሲሆን በሀምዛና በሂክማ መሳጂዶች ደግሞ የዱአ ተቃውሞ ተካሂዷል። በዙሪያዋ በሚገኙት ኤዶ፣ ሴሮስተ፣ ነጌሌ ሜጠማና ሌሎች የገጠር መንደሮችም የዱአ ተቃውሞ መደረጉ ተነግሯል።
ረቡእ እለት በዋለው ገበያ ሳይቀር ከፍተኛ የተቃውሞ ድምጽ አሰምታ የነበረችው ኮፈሌ ከተማም በአዲስ ከተማ ሰላም መስጊድ በተካሄደው ከፍተኛ የድምጽ ተቃውሞ የትግሉ አጋር መሆኗን በበርካታ መፈክሮች አጅባ አስመስክራለች። በሌላ በኩል በኮኮሳ ወረዳ ኮኮይሳ ከተማ ትልቁ መስጊድ ላይ የተስተናገደው ደማቅ የድምጽ ተቃውሞም እንዲሁ በርካቶችን ያሳተፈ የነበረ መሆኑ ተነግሮለታል።ለዋና ከተማዋ አዲስ አበባ ቅርብ በሆነችው አዳማ ከተማ አቡበከር መስጂድም ደማቅ ተቃውሞ ተደርጎ ውሏል። ከተቃውሞው መልስ የተወሰኑ ወጣቶች ታፍሰው እንደተወሰዱም ተሰምቷል።
በዛሬው የድምጽ ተቃውሞ ችግር ተፈጥሮ የዋለው በሻሸመኔ እና አዳማ ከተሞች ነበር። የሻሸመኔ ሰላማዊ ሙስሊም ማህበረሰብ በትልቁ መስጊድ በከፍተኛ ቁጥር ተሰብስቦ መፈክር ማሰማቱን፣ ብሶቱን መግለጹን ያልወደዱት የአካባቢው ታጣቂዎች ተቃውሞውን ለማስቆም ሰዎችን ያለርህራሄ ደብድበዋል። በርካታ የወታደር መኪኖችን በማምጣት መስጊዱን ለረዥም ወቅት ከብበው በመቆየትም በመስጊዱ ቅጥር ሆኖ ማንንም ሳይተናኮል ድምጹን የሚያሰማውን ሙስሊም ለማሸበርና ለማሸማቀቅ ሞክረዋል። በድብደባው ወቅትም በርካታ ሙስሊሞችን እያፈሱ በመኪና ሲጭኑ የአይን እማኞች ተመልክተዋል። በዚህ መልኩ ለተወሰነ ሰአት ከቆየ በኋላ የከተማይቱ አዛውንቶች ከታጣቂ ሀይሎቹ ጋር በመደራደር በሽምግልና ከበባውን ያስበተኑ ሲሆን በአምልኮ ስፍራቸው ታግተው የቆዩት ሙስሊሞችም በሰላም ወደየቤታቸው ተመልሰዋል። በዚህ ህገወጥ ድርጊት ያዘነው እና የተቀየመው የሻሸመኔ ማህበረሰብ ለታፋኞቹ ዱአ እያደረገ ይገኛል። ፖሊስ ያሰማራቸው ሰዎችም ድንጋይ ይወረውሩ እንደነበር ታይቷል፡፡
እንደ እስከዛሬዎቹ ጁምአዎች ሁሉ የዛሬውም ጁምአ አረጋግጦልን ያለፈው የተባበረ የህዝብ ድምጽ በአጓጉል ፕሮፓጋንዳ ሊሰናከል እንደማይችል ነው። መንግስት የህዝበ ሙስሊሙን ንጹህ ሀይማኖታዊ ጥያቄዎች በቀጥታ መልሶ የህዝቡን ድምጽ ከማክበር ይልቅ ነፍጥ አንግቶ መሳጂዶችን መቀማት፣ ሙስሊሞችን መደብደብና ከፍተኛ በደል ማድረስ ሰላማዊ ትግላችንን ሊገታውም ሆነ ሊቀለብሰው አይችልም። የሀይል እርምጃ ካሁን በፊትም በተለያዩ ቦታዎች ተሞክሮ ታይቷል፤ የህዝብን ድምጽ እና ቁርጠኝነት የበለጠ ከማጠንከር በስተቀርም ለበዳዮቻችን የፈየደላቸው ነገር የለም።
አዎን! መንግስት የፍትህ ጥሪ ድምጻችንን ቢያናንቅም እኛ ግን ታላቁ ጌታችን አላህ ሁሌም እንደሚሰማን እናውቃለን! በደላችንን የሚቆጥር እና ችላ የማይለን፣ የበለጠ በተስፋ የሚሞላንና ጥንካሬ የሚያላብሰንን ፈጣሪያችንን ተማምነን ድምጻችንን ማሰማት፣ ቁጣችንን መግለጽ እንቀጥላለን – በዳዮቻችን ቢጠሉም!
አላሁ አክበር!

No comments:

Post a Comment