Thursday, May 8, 2014

‘እኛና አብዮቱ’ በፍቅረሥላሴ ወግደረስ (ግምገማ፤ በታደለ መኩሪያ)


ካለፈው የቀጠለ ሁለተኛው ግምገማ፤ በታደለ መኩሪያ
በአሁኑ ግምገማዬ ከምዕራፍ 5 እስከ ምዕራፍ 13 ያለውን የመጽሐፉን ክፍል እዳስሳለሁ።
“ሻለቃ መንግሥቱ ኃይለማሪያም ‘በወታደር ሰፈር ተወልደው ከወታደር ጋር ያደጉ የወታደሩን ስነልቦናዊ አመለካከት በሚገባ የተረዱ መኮንን በመሆናቸው ፣የደርግ ሊቀመንበር ሆነው ተመርጠዋል።’ ገጽ 75 ፤ ገጽ 158 ላይ ደግሞ ‘ሻለቃ መንግሥቱ አገር ወዳድ ከመሆን አልፈው የሶሻሊዝምን ጽንስ_ሐሣብ በጥልቀት የተረዱ ባይሆንም፤ ሶሻሊዝም ለድሃው ኅብረተሰብ ክፍል ከፍተኛ ጠቀሜታ እንዳለው ስለሚያውቁ፤ ተማሪዎቹ ያቀረቡትን ጥያቄ በበጎ ዓይን ተመለከቱት” የደራሲውን የመሪያቸውን ተክለ ሰውነት ግንባታ ውጤት ገጽ 149 ላይ ታዩታለችሁ፤ ተከተሉኝ። New book by Fkreselase Wegderes
ምዕራፍ 5 ላይ ጄነራል ሚካኤል አማን አንዶም ኤታማዦር ሹመት በቀዳማዊ ኃይለሥላሴ ቢጸድቅም፤ አቅራቢው ሻለቃ መንግሥቱ ነበሩ፤ ያሉት ሁሉ ይሆናልና፤ ተክለ ሰውነቱ ከዚህ ይጀምራል። ብዙ ሳይቆይ እንዳልካቸው መኮንን ከሥልጣን ይወርዳሉ ወደእስር ቤት ይጣላሉ፤ ልጅ ሚካኤል እምሩን ይተካሉ፤ ብዙም አልቆዩም፤በፍቃዳቸው ሥልጣን ይለቃሉ፤ የገበጣ ጫወታ፤ በዓለም ከታወቁ የትምህርት ተቋማት የተማሩ ሊሒቃን adieu ከሥራ ውጭ ይሆናሉ። በመሻርና በመሾሙ የተኩራሩት ደርጎች ለንጉሡም አልተመለሱም፤ ሀገሪቱን እንደሚመሩ የልብ ልብ ተሰማቸው። ገጽ 83 ላይ የፓለቲካ እስረኞች እንዲፈቱም ለመጠየቅ በቁ፤ ጃኖሆይን ጠየቁ ፤ ንጉሡም አሾፉባቸው፤ አለማወቃቸውን ነገሯቸው፤ የሚገርመው ሀገር ሊመሩ የተዘጋጁት ደርጎች የለኢትዮጵያ የውስጥና የውጪ ጉዳይ ፈጽሞ የማያውቁ መሃይማን ናቸው። ደራሲው ያሳዩን ያንን ነው። በ1928 ዓ ም ኢጣሊያን ኢትዮጵያን በወረረችበት ወቅት አረጓዴ፣ ቢጫ፣ ቀዩን ስንደቃ አላማችንን አውርዶ የኢጣሊያኑን ሰንደቃ አላማ የሰቀለውን ኃይለሥላሴ ጉግሣን እንዲፈታ ስህተት መሆኑን በለዘበ ቃላት አስቀምጠው፣ ተማሪዎችንና የተለየ ዓላማ ያላቸው የተማሩ ሰዎች እንዳሳሳቷቸው አላከዋል፤ በተማሪዎች ንቅናቄ ዘመን ለጊዜው በሰልፉ ላይ ከተካፈሉት ውስጥ የታሰሩ ካሉ እንዲፈቱ ይጠየቃል እንጂ ‘የፓለቲካ እስረኛ ይፈታ’ የሚል ጥያቄ ቀርቦ አያውቅም ። በእርግጥ የንጉሡ አስተዳደር ለውጥ እንዲያደርግ መጽሐፍ በመፃፍ በአደባባይ ቅዋሜ በማሰማታቸው ዜጎች በግዞት መልክ ወደ ገጠር ክፍለ ሃገራት ተግዝዋል።ሆኖም ግን ኃይለ ሥላሴ ጉግሳ የፓለቲካ እስረኛ አልነበረም፤ ሡልጣን ኢብራሂም ዐሰብን እንደሸጠው የአጋሜን አውራጃ ለኢጣሊያ የሸጠ ሰው ነበር። ኃይለ ሥላሴ ጉግሳ በኢትዮጵያውያን ዘንድ የሚታወቀው በሀገር ካሃዲነትና በይሁዳነት ነው። ከዐፄ ቴዎድሮስ እስከ ቀዳማዊ ኃይለሥላሴ በተክለጻዲቅ መኩሪያ ገድ 230 መመልከት ይቻላል።በአምስተኛ ክፍል ሥረዓተ ትምህርት ውስጥ ይገኛል። ደራሲው ‘እኛና አብዮቱ’ መጽሐፋቸው ውስጥ ተባባሪ በሆኑበት መንግሥት ለተከናወኑት ተግባራት ቀጥተኛ ሃለፊነት ከመውሰድ ይቆጠባሉ። ይህንንም በየደረጃው አሣያለሁ።ደራሲውን አንድ የረሱትን ነገር ላስተውሳቸው በ1535 ዓም ጦርነት ከግራኝ ሙሐመድ ጋር መካሄዱን ገልጸው፤ ባሌን ያስተዳድር የነበረው አዝማች ደግለሃን ከግራኝ ጦር ጋር ሲዋጋ መሞቱን ዝንግተው፤ በባሌ ጎባ በሰሙ ‘አዝማች ደግለሃን’ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤተ የተሰየመለትን አንስተው ፤ በተራራ ሰይመውታል፤ ይህንን ድርጊት በማን ያሳብባሉ? ስለ ግራኝ ሙሐመድም የተዛባ ታሪክ አቅርበዋል፣ ስደርስበት አብራራለሁ።ከወዲሁ አንባቢዬ የግምግማዬን ዓለማ እንዲረዳልኝ ነው።
ምዕራፍ 6 የምናገኘው በሻለቃ መንግሥቱ ኃይለማሪያም የደርግ ሊቀመበርነት ፣በሻለቃ አጥናፉ አባተ ምክትልነት በሰማነያ አንድ ዓመት አረጋዊ ላይ የተፈጸመውን መፈቀለ መንግሥት ነው። ይህንን መስከረም 2፡ 1967 ዓ ም የተደረገውን መፈቀለ መንግሥት ሕዝቡ እንደደገፈው አጽንዎት ሰጥተው ይገልጹታል፤ በተቆጣጠሩት መገናኛ ብዙሃን በመጠቀም፤ ሃላፊነት በጎደለው ኢትዮጵያዊ ጨዋነት ባልታየበት ባህልን ባረከሰ መንገድ ንጉሡን አውርደው ታምር እንደሰሩ አጋነው ጽፈዋል። በወቅቱ ዜናውን በቴሌቪዥን የተከታተለው ሕዝብ ስለንጉሡ የተጠቀሱትን ነውሮች ተቀብሏቸው ይሆናል፤ ግን የመላው ሕዝብ ድጋፍ እንደላቸው አድርገው አቅርበውታል። ሙሉን ጽሑፍ ገጽ 110 መመልከት ይቻላል። በእርግጥ ሕዝቡ ለውጥ ፈልጓል፣ ግን ከየጦር ግንባሩ በምግባር ብልሹነት ይቀጡ ተብለው ከምድባቸው በተላኩ ወታደሮች የንጉሡን አስተዳደር እንዲተኩ አልነበረም፤ ‘ጊዜያዊ ሕዝባዊ መንግሥት ይቋቋም’ የሚለው መጠይቅ በወቅቱ በሠራተኛው ክፍል የቀረበው ለዚህ ነበር። መሣሪያ የታጠቀው ክፍል አልፈቀደም። ደራሲው ገጽ 116 ያሳዩን ከደሃ ቤተሰብ ስለመጣን ንገሡን ተክተን ሀገር እናስተዳድራለን የሚል እድምታ አለው። ውጤቱንም አየነው። ዛሬ ኢትዮጵያን እያስተዳደረ ያለው ወያኔም የሚለው ከአርባ ዓመት በፊት የተባለውን ነው። በቅርጽ ልዩነት ቢኖረውም በይዘቱ አንድ ነው። በትግራይ ሕዝብ ነፃነት ግንባር የተሰባሰበው ቡድን የቤሔር ቤሐረሰቦች መብት የቆምኩ ነኝ ይላል። የሕዝብ ጥያቄ ደግሞ ‘የሽግግር መንግሥት ይቋቋም’ ነው። ወታደሮቹ መፈቀለ መንግሥት ካደረጉ ይሄው አርባ ዓመቱ። ሀገራችን ከነበረችበት ቁልቁል ወረደች ሕዝባችን ተዋረደ እንጂ የተሻሻለ ነገር አልታየም ፤የሕዝብ ጥያቄ ገና አልተመለሰም።
ጄነራል አማን ርዕስ_ብሔር ሆነው መመደባቸው በበታች ማዕረግ ያለው ወታደር በተነገረው ተክለ ሰውነታቸው በመነሣት ወዷቸው ነበር፤ ከደርጉችም መካከል እንደዛው፤ ያም ሆኖ በአንዳንድ የጦር ክፍሎች ያሉ የንዑስ ደርግ አባላት ንጉሡ ከዙፋናቸው ከወረዱ በኋላ ‘ሕዝቡ ያሻውን መንግሥት ያቋቁም’ የሚል ተልኮ ነበራቸው፤ የመሐንዲስ፣ የአርሚ አቪዬሽንና የክቡር ዘበኛው የንዑስ ደርግ አባላት በምሳሌነት የሚጠቀሱ ናቸው።የነሻለቃ መንግሥቱ ተልኮ ግን ያ አልነበረም።ጅነራል አማን ሜካኤል አንዶም ቢሆኑም የራሳቸው አጀንዳ ነበራቸው።’እኔ አማን የግብፁ ጄነራል ነጂብ አይደለሁም። እኔን ለይስሙላ አስቀምጠው ሥልጣን በእነሱ እጅ ሊቆይ እይችልም’ ጅነራል አማን ያልተገነዘቡት ነገር ቢኖር መንግሥቱ በጎዘጎዘው መቀመጫ ላይ መቀመጣቸውን ነው። የወቅቱ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ ወያኔ በጎዘጎዘው መቀመጫ ላይ ምንም ማድረግ እንደማይችል እያየነው ነው፤ ታሪክ በኢትዮጵያ ላይ ራሷን ደገመች። ሻለቃ መንግሥቱ ኃይለማርያም፤ በየጦር ሠፈሩ ለሚነሳው ተቃሞ በ ማዳፈኛ ሰም ከሦስተኛ ክፍለ ጦር የሚቀርቧቸውን ቲፎዞ ሲያዘጋጁ፤ ትኩረት የሰጠው አልነበረም። ገጽ 122 ‘ይህ የክብር ዘበኛ ያሠራቸውን ሰዎች ባስቸኳይ የማይለቅ ከሆነ በአንበሳው ሦስተኛ ክፍለ ጦር እንደሚመታ ለምን አጠናክራችሁ አልነገራችሁም?! የመቶ አለቃ መላኩ ተፈራም ከክብር ዘበኛ ክፍል የመጣ ስለነበር እርሱም ለክፍሉ ተቆርቋሪነቱን በድፍረት አሣይቶ ነበር፤ ምን ያደርጋል እንደቴዎድሮስ ሊሆን ቃቶት የመደር አውደልዳይ፣ የሀገሩን ልጆች ገዳይ ሆኖ እርፍ አለው፤ ውሎ አድሮ ለመንግሥቱ ሎሌነት አደረ፤ ባለደረባዎቹን ሻምበል ደምሴ ሽፈራውን የመሰለ ኮፍጣና ወታደር አሣልፎ ሰጠ።
ኢትዮጵያ ከጥንታዊነቷ ጋራ በጣም ተገኖ በዓለም ሕዝብ ዘንድ የሚነገርላት ፍረሃ እግዚአብሔር ያለው ሕዝብ የሚኖርባት ሀገር መሆኑን ነው። የእስልምናና የክርስትና ሃይማኖት ተከታይ ሕዝቧ ለዓለም ሕዝብ አብነት መሆኗን ብዙ ደራሲያን የከተቡላት ሀገር ናት። መቻቻልን ለዓለም ያስተማሩ መሪ ንጉሥ ምኒሊክን ያፈራች ሀገር ነች፤ አነ ኔልሰን ማንዴላ የእርሳቸውን ፈለግ መከተላቸውን አይተናል። እምዬ ምኒሊክ የተዋጋቸውን የንጉሥ ተክሃይማኖትን ቁሱሉን በጋቢያቸው ጠርገው፤ ንጉሥ ጦናን ከዙፋናቸው ወርደው ቁሱሉን አጥበው፤ ሊወጋቸውን የመጣውን የኢጣሊያ ጦር ከማረኩት በኋላ እንደጠላት ሳይሆን እንደሰው ያሰተናገዱ ንጉሥ መሆናቸውን ዓለም የመሰከረው ነው፤ መልካምም መጥፎም መሪ ከሕዝብ ውስጥ ይወጣል፤ ሆኖም ስንዴውን ከእንክርዳድ መለየት ሕዝብ ሃላፊነት አለበት፤ ያንን ሃላፊነት ባለመወጣታችን ጥቂት ከየጦር ሠፈሩ የተሰባሰቡ ወታደሮች ሀገራችንን አዋረዱ የእኛን የአውሬነት ፀባይ በዓለም ፊት አሰሣዩት። ሕዳር 14 ቀን 1967 ዓ ም የሆነው ያ ነበር። በአንዲት ለሌት ወታደራዊ ደርግ በሚል ስም የተዋቀረ፣ ሕግ አራዊትነትን የተላበሰ ቡድን የፈጸመው ግድያ ነው። ከረባታቸውን አስረው ፍትህ አለ ብለው እጅ በሰጡ እውቅ ዜጎች ላይ ለተፈሰመው አረመኔዊ ግድያ እንደሕዝብ እንደሀገር ሐላፊነት ተቀብለን ቤሔራዊ እርቅ ግድ ይለናል። ይህን ካላደረግን በምንም ዓይነት ወደፊት ልንጓዝ አንችልም። የሚመጣው ትውልድ በሰቆቃ ሲደማ መኖር የለበትም። አድራጊዎቹም እንዲሆን የፈቀድንም፤ ከዚያን ድረጊት በኋላ የመንግሥቱ አካል ሆነን የሠራነውን ሁሉ የሚመለከት ስለሆነ ለቤሔራዊ እርቅ ዝግጁ መሆን አለብን። በቅርብ የዚህ ግድያ ተዋናኝ የሆኑት ፍቅረሥላሴ ወግደረስ ‘አኛና አብዮቱ’ በሚለው መጽሐፋቸው ከገባንበት አሻክላ ውስጥ የምንወጣበትን መንገድ አልጠቆሙም፤ በትውልድ ላይ የፈጠረውን ጠባሳ በሀገር ላይ ያደረሰውን ውርደት ገና አልተገለጸላቸውም፤ አጋጣሚውን ተጠቅመው ሰላም ለማስፈን አልፈለጉም። ገጽ 149 ‘በስድሳዎቹ ላይ የተላለፈው አሳዛኝ ውሳኔ’ ብለው ያቀርቡታል። የሟቾች ስም በዝርዝር ለማስቀመጥ እንኳን አልደፈሩም። በገጽ 275 ላይ ‘ኢሕአፓ የገደላቸው’ ብለው የ 271 ሰዎች ስም ዝርዝር አስፍረዋል። ያንን በሚቀጥለው ገጽ 84 ላይ ካቀረበት ሐቅ ጋር እያስተያየሁ እሄድበታለሁ። ደራሲው ለግድያው መንስኤ የጄነራል አማን የዕብሪት ባህሪ መሆኑን ሊያሳዩም ሞክረዋል። ገጽ 152 ላይ 59ኙ የግድያው ሰለባዎች የፖለቲካ እሥረኞች እንደሆኑ ይጠቅሳሉ፤ በእውነት ደራሲው የፖለቲካ እሥረኛ ምን እነደሆነ አሁንም የተረዱ አይመስሉም፤ ግን ይህን ያሉበት ምክንያት አላቸው፤ የመደብ ትግል ነው ያካሄድነው ለማለት ነው። ከድርጊቱ ራቅ ብለው ገጽ 192 የፃፉትን እነሆ ‘በደርግ ውሳኔ የአፄ ኃይለሥላሴ መንግሥት ከፍተኛ ባለሥልጣናትን መኳንንቶችና ጄኒራሎች ሲገደሉ ከማዘንና ከንፈር ከመምጠጥ ባሻገር ይህ አሳዛኝ እርምጃ ለምን ተወሰደ ብሎ በቁጭት በመነሳሳት በደርግ ላይ ጠመንጃ አንስቶ የሸፈተ አንድም የመሳፍንት ወይም የመኳንንት ወገን የለም’ የነዚህ ዜጎች ግድያ ኢትዮጵያን በዓለም ሕብረተሰብ ዘንድ ያላትን ክብር አሳጥቷታል፤ የደርግ መንግትሥትን በማውገዝ የዓለም ሕዝብ ከአጥናፍ አጥናፍ ድምፁን አሰምቷል፤ ዳራሲው ባይገልጹትም ያውቁታል፤ ፍትህን መጣስ ማለት ሰውን እንደሰው ያለመቀበል መሆኑን ሰው የሆነ ሁሉ የትም ይኑር የት የሚጋራው ነው፤ነፃነትና ሰው የአንድ ሳንቲም ሌላው ገጽጥታዎች ናቸው፤ ስለዚህ ፍትህ፣ሰውና ነፃነትም አንድም ሦስትም ናቸው። ስው አብሮት ከተፈጠረው ነፃነቱ በላይ የሚከባከበው ምን ሊኖር ይችላል? ፣ከስልሳዎቹ ግድያ በኋላ በአራቱም ማዕዘን ዜጎች መሣሪያ አነሱ፤ፍትህ በሀገሪቱ እንደሌለ ተገነዘቡ፤ መሬት በመወረሱ መሣሪያ ያነሳ ዜጋ አልነበረም፤ ደራሲው በምዕራፍ 10 ውስጥ ብዙ የተዘባ አውነትነት የሌለው ኢትዮጵያዊነትን ዝቅ የሚያደርግ ሐተታ አቅርበዋል፣ ለነፃነት የሕይወት ዋጋ ከፍለው ከቅኝ ገዥዎች ሀገራቸውን አስከበረው ያቆዩላቸው ልጆቻችው እቢ ለነፃነቴ ብለው መሣሪያ ያነሱትን ለቁራጭ መሬት ነው ማለት ስድብ ነው፤ የጅግና ሰም ማጥፋት ነው። ሕዝብ ለነፃነቱ እንጂ ለንብረት መሣሪያ አያነሣም፤ ደራሲው ደጃዝማች ፀሐዩ ዕንቁ ሥላሴ መሬቴ ስለተወረሰባቸው መሣሪያ አነሱ ሲሉ ጀግንነታቸው እንዴት ተረሳቸው? የመሬት አዋጅ፣ የእድገት በሕብረት ዘመቻ፣ የሶሻሊዝም ሥረዓት ማወጅ ከዚህ አረመናዊ ድርጊት ሰሜትን ለማስለወጥ የተደረጉ ነበሩ፤አሁን የምናየው ውጤት ይበልጥ ይናገራል። የድርጅቶች መፈልፈል፣የሱማሌ ወረራ፣የኤርትራ መገንጠል፣የወያኔ ለሥልጣን መበቃት መንስኤው የስልሳዎቹ ግድያ ነው። ለአንባቦዎቼ ለመግለጽ የምፈልገው ደራሲው ብዙ የሸሸጉን ነገር እንዳለ ነው። በስልሳዎቹ ላይ የሞት ውሳኔ ያሰተላለፉት የደርግ አባላት በአስራ አራቱም ክፍለሃገራት ተመሳሳይ ግድያዎችን መፈጸማቸውን አልነገሩንም፤ ደራሲው በጹፋቸው ሊያሳዩን የሞከሩት ዜጎች መሣሪያ ያነሱት በመሬት አዋጅ ተቆጥተው እንደሆነ ብቻ ነው። ኢሕአፓ (የኢትዮጵያ ሕዝብ አብዮታዊ ፓርቲ) ሕዳር 14 ቀን 1967 ዓ ም ግድያው ተከትሎ ደርግ ‘ፋሽሽት ነው’ ማለቱና የመሬት አዋጅን ተከትሎ ፋሽዝም ወደገጠር መስፋፋቱን ዲሞክራሲያ በሚለው ልሳኑ ለሕዝብ ማስነበቡን ገጽ 245 ላይ ገልጸዋል። ይህ ሐቅ ነው፤ ለምሳሌ ገጽ 199 ላይ የመንዝ ሕዝብ የደርግን ግድያ ተከትሎ ሕዝቡ ልጆቹን ከብቶቹን ነድቶ በረሃ መግባቱን ጽፈዋል፤ ይህ ሁኔታ ልክ 1928 ዓ ም የፋሽሽቱ ባንቱ ሞሶሎን በአየር ይህን ሕዝብ የደበደበበትን ወቅት ያስታውሰናል፤ ቦንብ ባይጥልም ሕዝቡ በከፈለው ግብር በተገዛ የጦር አይሮፕላን የማስፈራራቱ ተግባር ፋሽሽት ኢጣሊያ ከፈጸመው በምን ይለያል? በአይሮፕላኑ ጭኹት ነብሰ ጦሮች አስወርደዋል፤አረጋዊያን ተደናግጠዋል፤ ሕፃናት ስቅስቅ ብለው አልቅሰዋል፣ በረሃብ ሞተዋል፤ ታዲያስ ከ ፋሽዝም ሌላ ምን ሊባል ይችላል? ደራሴው ይህ ድርጅት፣ ከስልሳዎቹ ግድያ ውጪ ለተፈጸሙ ግድያዎች የንብረት ጥፋቶች ወዘተ ተጠያቂ ያደርጉታል፤ ወደፊት በሰፊው ስለአጠቃላይ ድርጅቶች በደርግ መንግሥት የተጫወቱትን አሉታዊና አዎንታዊ ሚና እገልፃለሁ።
ስለ ጄነራል ተፈሪ ባንቲ አሻሿም ትንሽ ከማለቴ በፊት ገጽ 125 ላይ የመሐንዲስ ንዑስ ደርግ ፤ ‘ሕዝባዊ መንግሥት ይቋቋም’ ፤ ‘ሠራዊቱ ወደ ጦር ሠፈሩ ይመለስ’ ማለቱ ይታወሳል፤ ይህን መጠይቅ በሊቀመበርነት ስለመራው፣ ተራ ወታደር በቀለ ወልደጊዮርጊስ ትንሽ ልበል፤ ከመስመር ወጥቼም ከሆነ አንባቢዎቼን ይቅርተ እጠይቃለሁ፤ ደራሲው ይህን ግለሰብ የኢ ሕ አ ፓ አባል አድርው አቅርበውታል፤ ከደራሲው አንድ አረፍተነገር ልዋስ ‘ለወጣቱ እውነተኛ ታሪክ ማስተማር’ የሚለውን ተመርኩዥ ፣ስለ ተራ ወታደር በቀለ ወልደጊዮርጊስ ትንሽ ልተርክ፣ ተራ ወታደር በቀለ ወልደጊዮርጊስ የሞተው ከጄነራል አማን ሚካኤል አንዶም ጎን ሆኖ ነበር፤ እነ ኮሎኔሌ ዳንኤል አስፋው የመሩትን ቡድን በመዋጋት የተሰዋ ወታደር ነበር። በቀለ አብሮ አደጌ ነው፤የኢጣሊያ ጦር በ1928 ዓ ም በኦጋዴን በኢልከሬ በኩል ወደመሐል ሀገር ሲገሰግስ በወቅቱ የሐርር ግዛት የነበረች ጊንር በምትባል ወረዳ መጋሎ በሚባል አካባቢ ለሳምንታት ትልቅ ጦርነት ይደረጋል፣ጣሊያ እንደመንጋ የምትነዳቸው አሽከሪዎችና የሱማሌ ምልምሎች በጅግንነት በተዋጋው ኢትዮጵያዊ ላይ በአየር ተደግፈው ጉዳት አደረሱበት፤ ከመጋሎ ከፍ ብላ ወይና ደጋው መሬት ላይ ከምትገኘው ቂንር ካለች ኮረብታ ሥር ከምትገኘው ጊንር ከተማ የተወለደ ነበር። ጃኖሆይ በአደበታቸው ጊንርም ተያዘ ብለው ጠይቀዋል እየተባለ ይነገራል።
እንዴትስ ልተኛ እንዴትስ ልረፍ፤
የአባቶታችን ደም ሲፈስ እንደጎርፍ፤
ዘምረው ካደጉት ትውልድ ነው።
ለሚሊሽያ የመለመሉት የባሌ ክፍለ ሃገር እንደራሴ የነበሩት ደጃዝማች ወርቁ እንቁሥላሴ ነበሩ።ከተማዋን ሊጎበኙ መጥተው ከከተማ ወረድ ብሎ ከሚገኘው የፀበል ወንዝ ስንዋኝ አይናቸው በቀለ ላይ ያርፋል።ራሱ በጣም ትልቅ ነው፣ ድጅኖ እንለዋለን፤ በጣም ዋነተኛ ነው፤ በብዛት ዝርዝሮችን ከወንዙ ሲበትኑልን በቀለ እየሰመጠ አላሲዘን አለ፤ የወር የሸንኮራና የሙዝ ባጀቱን ሳይዝ አልቀረም። በወቅቱ የሱማሌ ሠርጎ ገብ የክፍለ ሃገሩን ጸጥታ ያውክ ስለነበር በቀለ የአባቶቹን ፈለግ ተከትሎ የሀገር ወሰን ለማስከበር ሚሊሺያ ጦር ተቀጠረ። ከዚያም የአራተኛ ክፍለ ጦር በባሌ ክፍለሃገር የመሐንዲስ ቅርጫፍ ሲቋቋም ወደጦር ሠራዊት የተዛወረ ነበር። በቀለ ከልጅነቱ ጀምሮ በነፃነት መኖርን የሚወድ ጎደኞቹ የምንወደው ለመሪነት የምንመርጠው ነበር። በቀለ በማዕረጉ ተራ ወታደር ቢባልም በተግባሩ ከጄኒራል በላይ ነው።
በሌላው ዓለም ቢሆን ደርግ ከስልሳዎቹ ግድያ በኋላ ለአረመኔዊ ተግባሩ ፍርድ ከሚቀበልበት ሥፍራ ነበር፤ አልሆነም ፤ እንደመንግሥት ለመቀጠሉ እኛም እንደሕዝብ ተጠያቂነት አለብን።
ጄነራል ተፈሪ ባንቲ ለርዕሰ ቤሔርነት ጥቆማ ሲካሄድ የታዘብኩት ላካፍላችሁ።የአየር ኃይሉ ሻምበል ሲሳይ ሐብቴ ዝነኛ የነበሩትን በኢትዮጵያ ሕዝብ የሚታወቁትን ሌተና ኮሎኔል አምኃ ደስታን ይጠቁማል፤ ሻለቃ መንግሥቱ ኃይለ ማርያም ያንን ሳይረሱ እነ ሌተና ኮሎኔል ሌሎችም ባለከፍተኛ መዕረግ ባሉበት ግልፅ ውይይት እናድርግ ይላሉ፤ ሌተና ኮሎኔል አምኃ ስለመንግሥቱ ደካማ ጎኖች ይናገራሉ ‘አጥፍቶ መጥፋት’ በሚለው መጽሐፉ ፀጋዬ ገብረመድህን ተገልጾታል፤ ከዚያ በኋላ ሻለቃ መንግሥቱ እውቁን ተዋጊ ማኳሰሱን ይቀጥላል ፤ በመጨረሻም በከሸፈው መፈቀለ መንግሥት ይገለዋል። ጄነራሉም ከዚህ አያመልጡም፤ መልሰ መልሰን ያየነው ነው።Déjà vu!! የከርሞ ሰው ይበልን፤ በሦስተኛው ክፍል እንገናኝ።
ታደለ መኩሪያ
tadele@shaw.ca

No comments:

Post a Comment