Monday, May 12, 2014

በሜይ 8, 2014 በኦስሎ ከተማ ታላቅ ሰላማዊ ሰልፍ ተደረገ

ሜይ 8, 2014
ሔለን ንጉሴ/ኖርዌ

የዲሞክራሲያዊ ለውጥ በኢትዮጵያ ድጋፍ ድርጅት ኖርዌ የወያኔ መንግስት በኦሮሞ ተወላጆች ህፃናትን ጨምሮ በንፁሃን ዜጎች ላይ የፈፀመውን ግድያ በመቃወም በሜይ 8, 2014 በኦስሎ ከተማ ታላቅ የሰላማዊ ሰልፍ ተደረገ።


የዚህ ተቃውሞ ሰልፍ ዋና አላማ ህገመንግስታዊ መብታቸውን ተጠቅመው በሰላማዊ መንገድ ጥያቄያቸውን ባቀረቡ ወገኖች ላይ የወያኔ መንግስት ምላሹ ጥይት መሆኑና ከ40 በላይ ሰዎች ህፃናትንና ተማሪዎችን ጨምሮ ጭካኔ በተሞላበት በጥይት ደብድቦ መግደሉ ነው። ይህ ደግሞ ዛሬ በኦሮሞ ህዝቦች ላይ ብቻ የተፈፀመ ሳይሆን ከዚህም በፊት በአማራ ህዝብ ላይ በበደኖና በአርባጉጉ እንዲሁም በአኙዋክ ህዝቦች ላይ የጅምላ ግድያ የተፈፀመ በመሆኑ ይህንን ግፍ በመቃወም የተደረገ ሰልፍ ነበር። 


ዝግጅቱ በኖርዌጅያን የሰአት አቆጣጠር ከቀኑ 15፡00 ለሞቱት ወገኖቻችን የህሊና ፀሎት በማድረግ የተጀመረ ሲሆን ሰልፉም በተለያዩ መፈክሮችና በኢትዮጵያ ባንዲራ ያሸበረቀ ነበር። ኢትዮጵያውያኑም በወገኖቻችው ላይ የደረሰውን ግፍ በመቃወም በቁጣና በእልህ መፈክሮችን እየተቀባበሉ በአደባባይ ሲያሰሙ ውለዋል። የሰልፉ መጠናቀቂያ ስፍራ በሆነው በኖርዌጅያን ፓርላማ ፊት ለፊት ከተለያዩ ድርጅቶች የተወከሉ ተናጋሪዎች ወያኔ በህዝባችን ላይ እየፈፀመ ያለውን የሰብአዊ መብት ጥሰት ግድያን ጨምሮ ሲያወግዙና ሲኮንኑ ተሰምተዋል። በስፍራውም የኖርዌጅያን ፓርላማ ተወካይ በሰልፉ መሃል በመገኘት ድብዳቤያችንን ተቀብለው ለፓርላማ ለውውይት እንደሚቀርቡ ተናግረዋል። ሰልፈኛውም ኖርዌ በልማት ስም ለወያኔ የምትለግሰው ገንዘብ ህዝብ ለመጨቆኛና ለማፈኛ እንዲሁም የሰው ህይወት ማጥፊያ በመሆኑ የሚሰጠው እርዳታ እንዲቆም ጥያቄ አቅርበዋል።

በመጨረሻም የዲሞክራሲያዊ ለውጥ በኢትዮጵያ ድጋፍ ድርጅት ኖርዌ ሊቀመንበር የማጠቃለያ ንግግር ሲያሰሙ ወያኔ በህዝባችን ላይ እያደረሰ ያለውን የሰብአዊ መብት ጥሰት ድርጅታቸው የሚያወግዘው መሆኑን የሚገልፅ የአቋም መግለጫ በማቅረብና ለሞቱ ወገኖቻችን ቤተሰቦች መፅናናትን ተመኝተው የታሰሩ የኦሮሞ ተማሪዎች በአስቸኳይ እንዲፈቱና ይህንን ድርጊት የፈፀሙ አምባገነኖች በአስቸኳይ ለፍርድ እንዲቀርቡ ጠይቀው ስብሰባው በተያዘለት ሰአት በተሳካ ሁኔታ ተጠናቋል። 

ድል ለኢትዮጵያ ህዝብ

No comments:

Post a Comment