Thursday, March 27, 2014

ኢትዮጵያ፡ በቴሌኮም ላይ የሚደረግ ክትትል መብቶችን ያቀጭጫል


Ethiopia, Amhara Region, holy city of Lalibela, cyber cafe(በርሊን፤ መጋቢት 16 ቀን 2006 ዓ.ም) የኢትዮጵያ መንግስት በሃገር ውስጥ እና ከሃር ውጭ የሚገኙ ተቃዋሚዎች እና ጋዜጠኞች ላይ በስፋት የሚያካሂደውን የቴሌኮም ክትትል ለማጠናከር ከውጭ ሃገራት የሚገኝ ቴክኖሎጂ እንደሚጠቀም ሂዩማን ራይትስ ዎች ዛሬ ይፋ ባደረገው ሪፖርት ገለጸ፡፡
“ ‘የምንሰራውን ነገር ሁሉ ያውቃሉ’፡በቴሌኮም እና ኢንተርኔት የሚደረግ ክትትል
በኢትዮጵያ” የተሰኘው ባለ 100 ገጹ ሪፖርት የኢትዮጵያ መንግስት በሃገር ውስጥ እና ከሃገር ውጭ በሚኖሩ የፖለቲካ ተቃዋሚዎች ናቸው ተብለው በሚታሰቡ ሰዎች ላይ የሚያደርገውን ክትትል ለማስፈጸም ከተለያዩ ሃገራት በማግኘት ጥቅም ላይ ያዋላቸውን የቴክኖሎጂ ውጤቶች በዝርዝር አስቀምጧል፡፡ መንግስት የሚያካሂደው ይህ ክትትል ሃሳብን የመግለጽ፣ የመደራጀት እና መረጃ የማግኘት ነጻነቶችን የሚጥስ ነው፡፡ ኢትዮ ቴሌኮም በተሰኘው እና ሙሉ ባለቤትነቱ በመንግስት በተያዘው ብቸኛ የቴሌኮም አገልግሎት ሰጭ አማካኝነት መንግስት የሞባይል እና የኢንተርኔት አገልግሎትን ሙሉ በሙሉ መቆጣጠሩ ክትትል የማድረግ ስልጣኑን ባልተገባ መልኩ እንዲጠቀም ምቹ ሆኖለታል፡፡
በሂዩማን ራይትስ ዎች የቢዝነስ እና ሰብዓዊ መብቶች ዳይሬክተር አርቪድ ጋንሰን “የኢትዮጵያ መንግስት የቴሌኮም አገልግሎትን በመቆጣጠርየተቃውሞ ድምጾችን ለማፈን እየተጠቀመበት ነው” ብለዋል፡፡ አርቪድ ጋንሰን እንዳሉት “የኢትዮጵያን ህገወጥ የክትትል ተግባር ለማቀላጠፍ ምርቶችን እና አገልግሎቶችን እያቀረቡ የሚገኙ የውጭ ሃገራት ድርጅቶች የመብት ጥሰት ወንጀል ተባባሪ የመሆን እድላቸውን እያሰፉት ነው::”
ሪፖርቱ እ.ኤ.አ ከኖቬምበር 2012 እስከ ጃንዋሪ 2014 ዓ.ም. ባለው ጊዜ ውስጥ በኢትዮጵያ እና ሌሎች 10 ሃገራት የሚገኙ የጥቃቱ ሰለባዎችን እንዲሁም የቀድሞ የደህንነት ሠራተኞችን ባካተቱ ከ100 በላይ ቃለ-መጠይቆች ላይ የተመሰረተ ነው ፡፡ የቴሌኮም አገልግሎት ስርዓቱን መንግስት ሙሉ በሙሉ ስለሚቆጣጠረው የኢትዮጵያ የደህነነት ባለስልጣናትም ሙሉ በሙሉ በሚባል ደረጃ የስልክ ተጠቃሚዎችን የተቀረጸ የስልክ መልዕክት ልውውጥ ያለምንም ገደብ ያገኛሉ፡፡ አንድም ሕጋዊ ሥርዓት ሳይከተሉ ወይም ያለምንም የበላይ አካል ተቆጣጣሪነት በመደበኛነት እና በቀላሉ የስልክ ልውውጦችን ይቀርጻሉ።
ከታገዱ ድርጅቶች ጋር ግንኙነት አላቸው በሚል ተወንጅለው በዘፈቀደ የሚታሰሩ ሰዎች ላይ ህገወጥ ምርመራ በሚደረግበት ወቅት ከቤተሰብ አባላት እና ከጓደኞቻቸው ጋር ያደረጓቸውን እና በተለይም ደግሞ የውጭ ሀገራት ቁጥር ያላቸውን የተቀረጹ የስልክ ውይቶችን ያስደምጧቸዋል፡፡ በሰላማዊ የተቃውሞ ሰልፍ ወቅት የሞባይል ኔትወርኮች የሚዘጉ ሲሆን የተቃውሞ ሰልፍ ተሳታፊዎች የሚገኙባቸው አካባቢዎችም ከሞባይል ስልኮቻቸው በሚገኙ መረጃዎች አማካኝነት ተለይተው ይታወቃሉ፡፡
አንድ የቀድሞ የተቃዋሚ ፓርቲ አባል ለሂዩማን ራይትስ ዎች ሲናገር “አንደ ቀን አሰሩኝ እና ሁሉንም ነገር አሳዩኝ፡፡ ሁሉንም የስልክ ልውውጦቼን ዝርዝር ካሳዩኝ በኋላ ከወንድሜ ጋር ያደረኩትን የስልክ ንግግር አሰሙኝ፤ ያሰሩኝ በስልክ ስለፖለቲካ ስላወራን ብቻ ነው፤ ለመጀመሪያ ጊዜ የያዝኩት የራሴ ስልክ ነበርና ከዚያ በኋላ በነጻነት ማውራት የምችል መስሎኝ ነበር፡፡”ብሏል
መንግስት በኢትዮጵያ ፖለቲካዊ ጉዳዮች ላይ ማንኛውንም አይነት ነጻ እና ጠንከር ያለ ትንተና የሚያቀርቡ ድረ-ገጾችን በማገድ መረጃ የማግኘት ነጻነትን ገድቧል፡፡ ሂዩማን ራይትስ ዎች እና በኢንተርኔት ደህነንት እና መብቶች ላይ ምርምር የሚያደርገው የቶሮንቶ ዩኒቨርሲቲ ሲትዝን ላብ የጥናት ማዕከል ኢትዮጵያ ውስጥ በ2013 ዓ.ም ያደረጉት ሙከራ ኢትዮጵያ የተቃዋሚ ቡድኖችን፣ የመገናኛ ብዙኃንን እና የብሎገሮችን ድረ-ገጾች እንደምታግድ አረጋግጧል፡፡ ነፃ መገናኛ ብዙሃን እምብዛም በሌሉበት እንደ ኢትዮጵያ ባለ ሀገር ከድረ ገጾች የሚገኙ መረጃዎችን ማግኘት መቻል እጅግ ወሳኝ ጉዳይ ነው።
የኢትዮጵያ መንግስት በሞባይል ተጠቃሚዎች ላይ የሚያደርገው ክትትል ብዙ ጊዜ የኦሮሞ ብሔር አባል የሆኑ ሰዎችን ዒላማ ያደርጋል። በቁጥጥር ስር የዋሉ ሰዎች ለኦሮሞ ሕዝብ ሰፋ ያለ የራስ ገዝ አስተዳደር ለማጎናጸፍ የሚንቀሳቀሰው የኦሮሞ ነጻነት ግንባርን ከመሳሰሉ የታገዱ ድርጅቶች ጋር ግንኙነት ስለማድረጋቸው ወይም የእነዚህ ቡድኖች አባላትን በተመለከተ መረጃ እንዲሰጡ በማስገደድ የእምነት ቃል ለመቀበል የተጠለፉ የስልክ ልውውጦች ጥቅም ላይ ይውላሉ፡፡ በሃገሪቱ አወዛጋቢ የጸረ-ሽብር ህግ መሰረት በፍርድ ቤት ትእዛዝ መሰረት ስለመፈጸማቸው ምንም አይነት ማሳያ በሌለበት ሁኔታ የተጠለፉ የኢሜይል እና የስልክ ልውውጦች ለፍርድ ቤት በማስረጃነት ይቀርባሉ፡፡
ከኢትዮ ቴሌኮም ዳታቤዝ ውጭ በሆኑ የስልክ ቁጥሮች ከኢትዮጵያ ውጭ ስልክ የተደወለላቸው ግለሰቦች በቁጥጥር ስር ውለው ምርመራ ተደርጎባቸዋል። በዚህም ምክንያት በርካታ ኢትዮጵያዊያን በተለይም በገጠራማው የሃገሪቱ ክፍል የሚኖሩ ሰዎች ወደውጭ ስልክ ለመደወል ወይም ከውጭ ሃገራት የሚደወሉ ስልኮችን ለመመለስ ይፈራሉ፤ ይህ ደግሞ በርካታ ዜጎቿ በውጭ ሃገራት ስራ ላይ ለሚገኙባት ሃገር ከፍተኛ ችግር ነው፡፡
በኢትዮጵያ ያለውን የቴሌኮም አገልግሎት ለመቆጣጠር የሚውለው አብዛኛው ቴክኖሎጂ የሚቀርበው ዜድ ቲ ኢ ከተባለው የቻይናው ትልቅ የቴሌኮም ኩባንያ ሲሆን ኩባንያው እ.ኤ.አ ከ 2000 ዓ.ም ጀምሮ በሃገሪቱ ውስጥ የሚገኝ እና በተለይ ደግሞ እ.ኤ.አ ከ2006 ዓ.ም እስከ 2009 ዓ.ም ብቸኛ የቴሌኮም እቃዎች አቅራቢ ሆኖ የቆየ ነው፡፡ ዜድ ቲ ኢ በአፍሪካ እና ብሎም በዓለም ደረጃ የቴሌኮም ኢንዱስትሪ ከፍተኛ ሚና የሚጫወት ነው፤ በማደግ ላይ በሚገኘው የኢትዮጵያ ቴሌኮም ኔትዎርክ እድገትም ቁልፍ ሚና በመጫወት ላይ ይገኛል፡፡ ህገወጥ ከሆነ የሞባይል ክትትል ጋር በተያያዘ የሚፈጸሙ የሰብዓዊ መብቶች ጥሰቶችን ለመከላከል እርምጃዎችን በመውሰድ ላይ ስለመሆን አለመሆኑ ከሂዩማን ራይትስ ዎች ለቀረበለት ጥያቄ ዜድ ቲ ኢ ምላሽ አልሰጠም፡፡
በርካታ የአውሮፓ ኩባንያዎችም በተለይ በውጭ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያንን ዒላማ ለማድረግ የኢትዮጵያ መንግስት የሚጠቀምበትን ላቅ ያለ የስለላ ቴክኖሎጂ አቅርበዋል፡፡ በዩናይትድ ኪንግደም እና ጀርመን መቀመጫውን ካደረገው ጋማ ኢንተርናሽናል ኩባንያ ፊንፊሸር የተሰኘውን ቴክኖሎጂ እንዲሁም በጣሊያን መሰረቱን ካደረገው ሃኪንግ ቲም ኩባንያ ሪሞት ኮንትሮል ሲስተም የሚባለውን ቴክኖሎጂ ኢትዮጵያ አግኝታለች። እነዚህ ቴክኖሎጂዎች የደህንነት እና የስለላ ተቋማት የተጠቃሚዎችን ኮምፒውተሮችን ዒላማ በማድረግ በፈለጉት ጊዜ የኮምፒውተር ፋይሎችንና መረጃዎችን ለማግኘት እንዲሁም የዒላማውን እንቅስቃሴዎች ለመከታተል ያስችሏቸዋል። እነዚህ ቴክኖሎጂዎች ኮምፒውተሮችን በመክፈት፣ የማለፊያ ቃል (ፓሰዎርድ) በማስገባት እንዲሁም የኮምፒውተር ካሜራዎችን (ዌብ ካም) እና ማይክሮፎኖችን በመክፈት ኮምፒውተሩን ወደ ማዳመጫ መሳሪያነት መቀየር ያስችላሉ፡፡ በዩናይትድ ኪንግደም፣ በሰሜን አሜሪካ፣ በኖርዌይ እና በስዊትዘርላንድ የሚገኙ ኢትዮጵያዊያን በእነዚህ የኮምፒውተር ሶፍትዌሮች አማካኝነት ዒላማ ከተደረጉ ሰዎች መካከል ይገኙበታል፤ በሰሜን አሜሪካ እና ዩናይትድ ኪንግደም የኢትዮጵያ መንግስት ከፈጸማቸው ሕገወጥ የመረጃ ጠለፋዎች ጋር የተያያዙ ክሶች ለፍርድ ቤቶች ቀርበዋል። ዒላማ ከተደረጉ የኢትዮጵያውያን ኮምፒውተሮች የተወሰዱ የስካይፕ ንግግሮች የመንግስት ደጋፊ በሆነ ድረ ገጽ ላይ እንዲወጣ ተደርጓል።
የሰብዓዊ መብቶች ይዞታቸው ደካማ የሆነ መንግስታት የቴክኖሎጂ ምርቶቹን እንዳያገኙ ወይም እንዳይጠቀሙ የሚያግድ ትርጉም ያለው አሰራር ይኖረው እንደሆነ ሂውማን ራይትስ ዎች ለጋማ ጥያቄ ቢያቀርብም ኩባንያው ምላሽ አልሰጠም፡፡ ሃኪንግ ቲም በአንጻሩ ምርቶቹ ያለአግባብ ጥቅም ላይ እንዳይውሉ የተወሰነ ቅድመ ጥንቃቄ የሚያደርግ ቢሆንም እነዚህ ቅድመ ጥንቃቄዎች ለኢትዮጵያ መንግስት በተሸጡት ምርቶቹ ላይ ስለመተግበራቸው ሊያረጋግጥ አልቻለም፡፡
“ኢትዮጵያ በውጭ የሚገኙ የተቃዋሚ አባላትን ለማጥቃት የምትጠቀማቸው የውጭ ሃገራት ቴክኖሎጂዎች ቁጥጥር የሌለበት የዓለምዓቀፍ ንግድ ከፍተኛ አደጋ እየፈጠረ ስለመሆኑ የሚያሳይ አደገኛ ምሳሌ ነው” ያሉት ጋንሰን “የእነዚህ መሳሪያዎች እና ቴክኖሎጂዎች አምራቾች መሳሪያዎቹ ያለአግባብ ጥቅም ላይ እንዳይውሉ የሚያስችሉ አስቸኳይ እርምጃዎችን መውሰድ እንዲሁም በውጭ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያንን ዒላማ ለማድረግ ስራ ላይ ስለዋለው ቴክኖሎጂ ምርመራ ማድረግ እና በኢትዮጵያ የሚያካሂዱት ስራ የሰብዓዊ መብቶች ላይ የሚያደርስውን ተፅዕኖ መፈተሽ አለባቸው፡፡” ብለዋል።
እንዲህ አይነት በጣም አደገኛ የስለላ ሶፍትዌሮች በዓለም ዓቀፍ ደረጃ ምንም ዓይነት ቁጥጥር አይደረግባቸውም እንዲሁም በሃገራት ደረጃ ያለው ቁጥጥርም በቂ አይደለም አልያም የውጭ ሽያጫቸው ላይ ገደብ አይጣልም በማለት ሂዩማን ራይትስ ዎች ይገልጻል፡፡ በ2013 ዓ.ም. በመብት ጉዳዮች ላይ የሚሰሩ ቡድኖች ጉዳዩን አስመልክቶ ለኢኮኖሚ ትብብር እና ልማት ድርጅት (ኦኢሲዲ) አቤቱታ ያቀረቡ ሲሆን አቤቱታው እንዲህ አይነት ቴክኖሎጂ በባህሬን የሚገኙ የመብት ተሟጋቾችን ለመከታተል ጥቅም ላይ ውሏል፤ ሲትዝን ላብ መሳሪያዎቹና ቴክኖሎጂው ከ25 በላይ ሃገራት ጥቅም ላይ እንደሚውሉ የሚያሳይ ማስረጃ አግኝቷል የሚል ነው፡፡
በዓለም ዓቀፍ ደረጃ ጥበቃ የሚደረግላቸው የግላዊ ጉዳይ፣ ሃሳብን የመግለጽ፣ መረጃ የማግኘት እና የመደራጀት መብቶች በኢትዮጵያ ሕገ መንግስት ውስጥም ተካተዋል፡፡ ነግር ግን የኢትዮጵያ መንግስት የሚያካሂደውን ህገወጥ ክትትል ለመከላከል የሚያስችል የህግ አውጭ እና የህግ ተርጓሚ አካላት የሚከተሉት አሰራር የለም ወይም ብዙም ዋጋ አይሰጠውም። አደጋውን የበለጠ የከፋ የሚያደርገው ደግሞ በኢትዮጵያ እስር ቤቶች በሚገኙ የፖለቲካ እስረኞች ላይ በስፋት የሚፈጸመው ማሰቃየት እና ያልተገባ አያያዝ ነው፡፡
ኢትዮጵያ ክትትል የማድረጊያ ቴክኖሎጂዎችን የምትጠቀምበት መጠን ውሱን የሚሆነው በአቅም ምክንያት ወይም በቁልፍ የሚኒስቴር መስሪያቤቶች ላይ ሙሉ እምነት ለማሳደር ካለመቻል ጋር የተያያዘ ሊሆን እንደሚችል ሂዩማን ራይትስ ዎች ገልጿል፡፡ ሆኖም ይህ አቅም ይበልጥ እያደገ በመጣ ቁጥር በሞባይል እና ኢሜይል ላይ የሚካሄደው ህገ ወጥ ክትትል የበለጠ ሊሰፋ ይችላል።
በርካታ ኢትዮጵያዊያን መንግስት ፍጹም የሆነ ክትትል የማድረግ አቅም እንዳለው ስለሚያስቡ ራሳቸውን በከፍተኛ ሁኔታ ሳንሱር የሚያደርጉ ሲሆን ይህም ኢትዮጵያዊያን በቴሌኮም ኔትዎርኮች ላይ በተለያዩ ርዕሶች ዙሪያ በሚያካሂዱት ውይይት ሃሳባቸውን በግልጽ ከመሰንዘር እንዲቆጠቡ በማድረግ መንግስት በተጨባጭ ማድረግ ከሚችለው በላይ ቁጥጥሩ የከፋ ተጽእኖ እንዲኖረው አድርጓል። የሞባይል አገልግሎት ሽፋን እና የኢንተርኔት አገልግሎት እጅግ ውስን በሆነበት በተለይ በገጠሩ የኢትዮጵያ ክፍል ራስን ሳንሱር ማድረግ የተለመደ ሆኗል፡፡ ዋናው የመንግስት የመቆጣጠሪያ መንገድ በጣም ሰፊ የሆነው የመረጃ አቀባዮች መረቡ እና እስከታች የማህበረሰብ ስርዓት ድረስ የተዘረጋው የክትትል መንገዱ ነው፡፡ ይህም አብዛኞቹ በገጠር የሚኖሩ ኢትዮጵያዊያን የሞባይል ስልኮችን እና ሌሎች የቴሊኮምዩኒኬሽን ቴክኖሎጂዎችን እንደ ተጨማሪ የመቆጣጠሪያ መሳሪያ አድርገው እንዲያዩ እንዳደረጋቸው ሂዩማን ራይትስ ዎች ለመረዳት ችሏል፡፡
ጋንሰን እንዳሉት “የኢትዮጵያ የቴሌኮም አገልግሎት እያደገ በሄደ ቁጥር አስፈላጊው የህግ ጥበቃ እንዲተገበር እና የደህንነት ሰራተኞች በሰዎች ግላዊ ግንኙነቶች ላይ ያልተገደበ ክትትል እንዳያደርጉ ያለው አስፈላጊነትም ይጨምራል፡፡” “የሞባይል እና የኢንተርኔት ቴክኖሎጂዎች ወደ ሃገር ውስጥ ሲገቡ ዴሞክራሲን ለመደገፍና የሃሳቦች እና አስተያየቶች ስርጭትን እንዲሁም ሃሳብን የመግለጽ ነጻነትን የበለጠ በሚያመቻች መልኩ እንጂ የህዝብን መብት ለማፈን ጥቅም ላይ መዋል የለባቸውም፡፡”

No comments:

Post a Comment