Wednesday, March 12, 2014

የብርሃኑ ዳምጤ (አባመላ) ቅልቅል


ክንፉ አሰፋ
ብርሃኑ ዳምጤ እንደገና ሲገለበጥ የአስር አመት ልጅ ሳለሁ ያጋጠመኝን አንድ ክስተት አስታወሰኝ። በሰፈራችን ውስጥ ልጆችን ሁሉ የሚጠሉ አንድ ሰውየ ነበሩ። አንድ ቀን በድንገት ተነሱና የሰፈሩን ሰው ሁሉ መሰናበት ጀመሩ። በእጃቸው 3 ሜትር የሚያህል ርዝመት ያለው ገመድ ይዘዋል። “የሰፈሩ ልጆች ስላስቸገሩኝ ራሴን ልስቅል ነው። ደህና ሁኑ…” እያሉ ሁሉንም ተሰናብተው ሲያበቁ ለመሰቀል መንገዳቸውን ጀመሩ።  የእኝህ ሰው ውሳኔ ለመንደሩ ሰው ሁሉ ደንታ አልሰጠውም።ESAT brings Aba Mela as a political analyst
የሰፈር ልጆች ግን ተከተልናቸው። ብዙ ነበርን። ሰውየው ተራራ ሲወጡ አብረን ወጣን።  ቁልቁል ሲወርዱም አብረን ወረድን። ጉዞው አሰልቺ ነበር። ግን ተስፋ ሳንቆርጥ ጉዱን ለማየት ስንል ተከተልናቸው።  በመጨረሻ አንድ ዛፍ አገኙና የሚሰቀሉበትን ገመድ እዛፉ ላይ ማሰር ጀመሩ።
ሰው ሲሞት አይተን ስለማናውቅ ሁኔታውን እንደ ልብ አንጠልጣይ ፊልም ነበር በጉጉት የምንከታተለው። ሰውዬው በዚህ ሁኔታ ለመሞት መወሰናቸው ብዙም አላስደነገጠንም። ይልቁንም  ከኛ እየቀሙ በግቢያቸው ያጠራቅሙዋቸው ኳሶቻችን ነጻ ሊወጡልን ነው ብለን ተደስተናል።
ገመዱን አስረው ራሳቸውን ለመሰቀል ካመቻቹ በኋላ ዘውር ብለው እኛን ተመለከቱን። «እባኮን ይተው!» የሚላቸው አንድ እንኳን ሰው አልነበረም።  ለደቂቃዎች በአትኩሮት ከተመለከቱን በኋላ እንዲህ አሉ።  «እንዲያውም ደስ አይበላችሁ። ሃሳቤን ቀይሬአለሁ። አልሰቀልም!»
ዛፉ ላይ ያሰሩትን ገመድ ፈቱትና ወደ ሰፈር አቀኑ። ካልተሳከው የጎልጎታ መሰውያ ሲመለሱ እመንገድ ላይ ያገኛቸው አንድ ሰው ሲመክራቸው ሰማን።  «ሌላ ግዜ መሰቀል ከፈለጉ ለሰው አይናገሩ። ድምጽ አጥፍተው ለብቻዎ ያርጉት። የዚህ ሰፈር ልጆች አብዝተውታል።  ሰው በሰላም እንኳን እንዳይሞት እያደረጉ ነው።»
ሰውየው ለመካሪያቸው ምንም ምልስ አልሰጡም- ግን ወደኛ እየተገላመጡ  «እርሱት። አታገኙዋትም!» የማለት አይነት በአይናቸው እየዛቱብን እቤታቸው ገቡ።
ከልጅ ጋር የሚጫወቱት እንቁልልጬ መሆኑ ነው። ለዚያማ ማን አክሎን። የባሰ እልህ ውስጥ አስገቡን። … በመጨረሻ ብቻቸውን መንገድ ላይ እያወሩ መሄድ ሲጀምሩ ተውናቸው። …
የሳይበሩ አንበሳ የመታጠፉ ፍጥነት ሳይገርመን የድጋሚ ቅልቅሉን በከአዲስ ዜማ አከለበት።  ”እንደውም ደስ አይበላችሁ። ወያኔን ተቀላቅያለሁ!” የሚል ዜማ።  የልጅነት እንቁልልጬ ጨዋታ ይመስላል።  ለመዞርማ ምድርም ብርሃንና ጨለማን ለማፈራረቅ በራስዋ ዛቢያ ላይ ትዞራለች።  የኋላውን ለማየት ሲል አንገትም ይዞራል። ብረትም ይዞራል – በእሳት ሲፈተን። … ቆርቆሮ ግን እንዲሁ ይጠመዘዛል።
«..እኔ እንኳን ትንሽ መቆየት ፈልጌ ነበር።» አለ ኦቦ ዳምጤ፤ ለሁለተኛው ዙር ከወያኔ ጋር ያደረገውን ቅልቅል ሲያበስር። ይህችን አነጋገር የተጠቀመባት ያለ ምክንያት አልነበረም። ወደዚህኛው ጎራ የገባው የጥምር ሰላይ (double agent) ስራ ለመስራት እንደሆነ ለማስመሰል መሞከሩ ነበር።  ፈረንጆቹ (match fixing) ማች ፊክሲንግ የሚሉት በእግር ኳስ አለም ውስጥ ለተቃራኒው ተገዝቶ የመስራት ውስልትና አይነት መሆኑ ነው። እንዲህ የተራቀቀ ቢሆንማ ኖሮ እናደንቀው ነበር። ግና በዚያው ቃለ-ምልልስ ላጠፋው ጥፋት ይቅርታ ጠይቆ ጨዋታውን አበላሸው። ድንጋይ በትከሻው ባይሸከምም ህሊናውን ዝቅ አድርጎ ከአክራሪ ዲያስፖራ ጋር በመዋሉ በጣም ተሰምቶታት።  ወያኔዎች ይቅርታ የሚላቸውን ለምን እንደሚወዱ አይገባኝም።  ይቅርታ የሚጠይቋቸውን ሰዎች በጣም ሲወድዱ እንጂ ምህረት ሲያደርጉላቸው ግን አይተን አናውቅም።  ታምራት ላይኔን በፓርላማ ካዋረዱት በኋላ ቀፈደዱት። ሰለሞን ተካልኝም ከይቅርታ አልፎ ከዲያስፖራው ርኩስነት ለመጽዳት ሲል አባን ጸበል እርጩኝ ብሎ ነበር – በዘፈን። መቀሌ ድረስ ሄዶ በኢህአዴግ ጸበል ቢጠመቅም፣  እነሱ ግን ቂማቸውን አልረሱም። ሁሉንም ማኖ እያስነኩ በአየር ላይ ያንሳፍፏቸዋል።
አባመላ ከነሱ ጋር ተጣልቶ ወደ ተቃውሞ ጎራ በሄደ ጊዜ ወያኔዎች አንድም ነገር አልተነፈሱም ነበር። ምክንያቱም ጸቡ የመርህ እንዳልነበር ያውቁታል። ጉዳዩ የግል ጥቅም ነው። መፍትሄውም ቀላል። በፈለጉት ግዜ እንደ ቆላ በሬ አሞሌ ጨው አልሰው እንደሚመልሱት አስቀድመው ያውቁታል።
በቃለ-ምልልሱ አባ መላ በካፒቴን ሀይለመድህን አበራ ዙርያ የተነሳውን ክርክር ሊቋቋመው እንዳልቻለ አልካደም።  በክርክር ሲሸነፍ እንደመፍትሄ የወሰደው የወያኔን ጎራ መቀላቀል መሆኑም አዲስ ነገር አይደለም። ያኛው ጎራ በሃሳብ የተሸነፉ መሃይማን መሰብሰብያ ጎራ ከሆነ ሰንበትበት ብሏል።
ንግግር መቻል አንድ ነገር ነው። እየቀለዱ ሰውን ማሳቅም ቀላል ሊሆን ይችላል። በመናገር ሰዎችን ማሳመን መቻል ግን ሌላ ጉዳይ ነው። ይህ ጥበብን፣ ብስለትን እና አስተዋይነትን ይጠይቃል። በንግግር ሰዎችን ማሳመን መቻል ደግሞ ሮኬት ሳይንስ መሆንን አይጠይቅም። አንዳንዶች በትምህርት ያገኙታል። ሌሎች በማንበብ ይለወጣሉ። የህይወት ተመክሮም በራሱ ብዙ ነገር ያስተምራል። ከስህተታቸው እየተማሩ የሚበስሉ ሰዎችም ብልሆች ናቸው።
«አቶ መለስ ዜናዊ እድሜ ልካቸውን የአማራን ህዝብ ሲሳደቡ ሰንብተው፤ አንድ አማራ ሲሰድባቸው ግን ደግም ላይመለሱ አሸለቡ።» የሚል ቀልድ ሰምቼ በጣም ነበር የሳቅኩት። ነገሩ ልክ ነው። በሌላው ላይ የሚቀልዱ ሰዎች በራሳቸው ላይ ሲደርስ በቶሎ ይሰበራሉ ይባላል።
እናም በሃይለመድህን ጉዳይ «ከጽንፈኞች» ሳይስማማ በመቅረቱ የጠፋው በግ ወደ ቤቴ ተመለስኩ ነው እያለን ያለው። ይህ ሰው ግን ስንት ጊዜ ነው ከቤቱ የሚጠፋው?
ደግሞ ፍጥነቱ። የብርሃን ጉዞም እንደብርሃኑ ዳምጤ አይፈጥነም። ወደዚያኛው ጎራ ሲቀየስ የለበሰውን የዲያስፖራ ማልያ እንኳ ለመለወጥ ግዜ አልወሰደም።  የቡናን ማልያ ለብሶ ለደደቢት የሚጫወት አይነት ሰው ነው የሆነው።
እንደዚህ አይነት ሰዎች ስብእናቸውን የሚሸከም አንገት ስለሌላቸው ወደግራም ሆነ ወደቀኝ፣ ወደፊትም ሆነ ወደኋላ ለመተጣጠፍ ችግር የለባቸውም።  ይህ ሰው ወደ ቀኝ ታጥፎ በነበረበት ግዜ ከአንዴም ሶስቴ ደውሎ በስልክ አናግሮኝ ነበር። አቀራረቡ፣ አነጋገሩና ጨዋታው ያራዳ ልጅ ይመስላል። ተግባሩ ግን የአራዳ ልጅ አይደለም። ያራዳ ልጅ ባልንጀራውን ይረዳዋል እንጂ በቁሙ ሊያርደው አይዳዳም።
ወያኔ የመሆን መብቱ እንደተጠበቀ ሆኖ ይህንን ለመሆን የሄደበት መንገድ ግን በጣም ይደብራል። ድርጊቱ ሰሞኑን በፈረንሳይ ሃገር ከተፈጸመው አሰቃቂ ግድያ ጋር ተመሳሳይ ነው የሆነብኝ። የክህደት ትንሽ የለውም።  ልዩነቱ አባ መላ ያስጠጉትን ወገኖች በቁም አለመግደሉ ብቻ ነው።
አንዲት የዋህ ወይዘሮ፤ በፓሪስ ከተማ እመንገድ ላይ ወድቆ የሚለምን ኢትዮጵያዊ ወገን አግኝተው እጅግ አዘኑለት። እቤታቸውም ወስደው ማረፍያ ሰጡት። መሰረታዊ የሆነውን ነገር ሁሉ አሟሉለት። አምነው ያሳደሩት ይህ ሰው ግን ውለታቸውን በአሰቃቂ ሁኔታ መለሰላቸው።  አራት ወር እንደቆየ ይህንን የሶስት ልጆች እናት ከትንሽ ልጃቸው ጋር በሴንጢ አርዶ ተሰወረ። አባመላ አብረውት ሲሰሩ የነበሩትን በቢላ ባያርዳቸውም በአነጋገሩ ስጋቸውን እንደበላው ነው የሚቆጠረው።  አምነው አስተጉት  ይህ ሰው እንደጴጥሮስ ጎህ ሳይቀድ ካዳቸው። የክህደት ቁልቁለት ይሏል እንዲህ ነው።  «የተናገሩት ከሚጠፋ የወለዱት ይጥፋ!» ይላሉ አበው።  ቃልን ማጉደል ምን ያህል ከባድ ነው!
ታማኝ በየነ እና አበበ ገላው ከብርሃኑ ዳምጤ ጋር በሳውዲው ቀውስ አብረው መስራት ሲጀምሩ በፍጹም ቅንነት እና በየዋህነት ነበር። ይህንን በማድረጋቸውም በርካታ ትችት ቀርቦባቸዋል። እነሆ አባ መላ ዛሬ ለቅልቅሉ እጅ መንሻ እነሱን በመሳደብ እንደመስዋዕት አቀረባቸው።
የብርሃኑ ዳምጤ አካሄድ ያሳሰባቸው ሁለት ወዳጆቼ በዚያን ሰሞን በዚሁ ጉዳይ ላይ በሰል ያለ አስተያየት ጽፈው ነበር።  በልጅግ ዓሊ (ከፍራንክፈርት) እና እንግዳሸት ታደሰ (ከኦስሎ)።  እነዚህን ጽሁፎች እንደገና እንድታነቧቸው እመክራለሁ።  በልጅግ ዓሊ «ዘመንን ለማሰር» በሚለው ጽሁፉ ይህ ሰው እንደ ጴትሮስ ይክደናል ነበር ያለው።
…ለአንዲት የሰሙኑ የፖለቲካ ጥቅም ሲባል ብርሃኑ ደቡርን እላይ የሰቀላችሁት በኋላ እንደለመደው ሲክዳችሁ ስትንጫጩ መስማታችን አይቀርም። ትንቢት እንዳይመስላችሁ ደቡርን በደንብ አድርገን እናቀውቀዋለን። ቆዳችሁን ገፎ ይሸጠዋል፣ ደቡር ሃገሩን አይደለም እናቱንም ቢሆን ይደልላል። አታውቁት እንደሆን መርካቶ ላይ ሄዳችሁ የተሰራውን ግፍ ጠይቁ። እንኳን የቀይ ሽብሩን ፣ እነ ሽብሬን ረስተን የለም እንዴ !!  ምን ይደንቃል።
ብሎ ነበር። እንግዳሸት ታደሰ ከኖርዌይ የጻፈውም ተመሳሳይ ነገር ነበር። «አባ መላ ልብ ሲበላ! » በሚለው መጣጥፉ «የዲያስፖራ ኃይል በአራዳ ስልትና በወያኔ ቆረጣ ለመሰንጠቅ ፣ የሚደረግም ጨዋታ ሊሆን ይችላል ብሎ መገመትም የዋህነት አይመስለኝም።» ነበር ያለው።  እነዚህን መጣጥፎች ደግሜ ሳነባቸው ትንቢት ነው የመሰሉኝ። በወቅቱ ግን እነዚህን ጽሁፎች በድረገጽ በማውጣቴ የስድብ ናዳ ወርዶብኝ ነበር።  አንዱ የፓልቶክ ታዳሚ እንዲህ ብሎ ነበር የጻፈልኝ። «የማናውቅህ እንዳይመስልህ! አንተ የዳዊት ከበደ ወንድም!»
የትኛው ዳዊት እንደሆነ ግን ግልጽ አላደረገልኝም። የአትላንታው ወይንስ የአውራምባው?
እርግጥ ነው። በፖለቲካ ቋሚ ወዳጅ ወይንም ቋሚ ጠላት የለም -  ጥቅም እንጂ። በመርህ ላይ ሳይሆን ይልቁንም ለግል ጥቅም ሲሉ የሚዋዥቁ ሰዎች ናቸው ሀገርን የሚያጠፉት። በተለምዶ መሃል ሰፋሪዎች ይባላሉ። እንደዚህ አይነቶቹ  ሰዎች በተቃዋሚውም ጎራ ነፍ ናቸው። ደጋፊ ሳይሆን ተደጋፊ ሆነው ለመኖር ሲሉ ብዙ ጥፋት ይሰራሉ። የሃይል ሚዛኑ እስካዘነበለ ድረስ ለአለቆቻቸው እጅግ ታማኝ ይሆናሉ። የሃይል ሚዛኑ ሲዛባ ደግሞ ለመካድ የመጀመርያዎቹ ናቸው።
ይህ የመርካቶ ቁጭበሉ ሼም አያውቅም። ትንሽ ብትጠብቁት እንደገና ይመለሳል። በዚህ አይነት ሰው ላይ እምነት መጣል እና መስጋት ከየዋህነት ያለፈ ነው።  አንድ ጅል ትምህርት ቤት ሲሄድ የሙዝ ልጣጭ አዳልጦት ወደቀ። ከትምህርት ቤት ሲመለስ ያችኑ የሙዝ ልጣጭ አይቶ ቆመ። ከዚያም ማልቀስ ጀመረ።  ለምን እንደሚያለቅስ ሲጠየቅ ወደ ልጣጩ እያመለከተ እንዲህ አለ። «እንደገና ልወድቅ ነው።»

No comments:

Post a Comment