Thursday, November 28, 2013

ዶክተር ሀይሉ የተቃዋሚዎችን ድክመት በድፍረት ተናገሩ

    
የዛሬዋ ኢትዮ ምህዳር ስለ ተቃዋሚዎች ውህደትና ህብረት ሰፊ ሀተታ ይዛ ወጥታለች፡፡ በተለይ ዶክተር ሀይሉ አራዕያ ስለ ተቃዋሚዎች ውህደት ያነሱት ሀሳብ ወቅታዊና አንገብጋቢ ሆኖ አግኝቸዋለሁ፡፡
ዶክተር ሀይሉ የተቃዋሚዎችን ድክመት በድፍረት ጽፈዋል፡፡ ዶክተሩ ተቃዋሚዎች ካልተዋሃዱ፣ ካልተባበሩ በስተቀር ምርጫ ሊያሸንፉና ለውጥ ሊያመጡ እንደማይችሉ አስረግጠው ነግረዋቸዋል፡፡ ዶክተሩ የሚሉት ለስልጣን ሳይሆን ለህዝብ ተዋሃዱ፣ ካለፈው ስህተት፣ ከሌሎች አገራትም ተማሩ፣ ህዝብን አታስገዙ፣ ጥቂት ተስፋ ሰጥታችው ዋናውን ተስፋውን አትንጠቁ ነው፡፡
እንደ እሳቸው አባባል ግን የተቃዋሚው ጎራ ለመዋሃድ የሚያስችል አላማም ሆነ ወኔ አይታይበትም፡፡ እስካሁን ያዳከመውና፣ ህዝብን ተስፋ ያስቆረጠውም ይህ አመሉ ነው ይላሉ፡፡ ለዚህ ሁሉ መፍትሄ ያሉትን ሁሉ በሰፊው ተንትነዋል፡፡ እንደ እኔ ዶክተሩ ያነሱት እጅግ ወቅታዊ ጥያቄ ነው፡፡ አጀንዳውን ያነሱትም በገለልተኝነት መሆኑን ከጽሁፋቸው መረዳት ይቻላል፡፡ ውጥንቅጡ ለወጣው የተቃዋሚው ጎራም ከዚህ ውጭ መፍትሄ ያለው አይመስለኝም፡፡ ዶክተሩ ጉዳዩን በሚዲያ ብቻ ሳይሆን ለተቃዋሚዎች እንዲወያዩበትም መድረክ አዘጋጅተው አቅርበውታል፡፡
የዶክተሩን ጩኸት የሚሰማቸው ከተገኘ በተቃዋሚው ጎራ መልካም ነገር እንደሚኖር የሚጠበቅ ነው፡፡ ግን ይች በተናጠል ሰላማዊ ሰፍል ከመጥራት፣ አዳራሽ ውስጥ በጥቂት ሰዎች ስብሰባ ከማድረግ፣ መግለጫ ከማውጣት፣ በዓመት አንድ ቀን በኢቲቪ ከመከራከር ውጭ ግብ የሌላቸው በርካታ ፓርቲዎች በተሰበሰቡበት ማን ይሰማቸው ይሆን? እጅ መጠቋቆሙን፣ መጠላለፉን፣ ግለሰብ ማግነኑን እንደ ትልቅ ስኬት የሚያዩት፤ ከህዝብ ስልጣን ይልቅ ‹‹ፓርላማ›› ለመግባት የሚቋምጡት ‹‹ፖለቲከኞች›› ያዳምጧቸው ይሆን? ምሁራን ምን ያህል ይደግፏቸዋል?
የጥናቱን ሶፍት ኮፒ ያገኛችሁ ኢትዮ ምህዳርን ለማያገኙ ኢትዮጵያውያን ፌስ ቡክ ላይ ብትለጥፉላቸው መልካም ነው፡፡

Getachew Shiferaw

No comments:

Post a Comment