Thursday, June 13, 2013

ከአረብ ሃገራት ሰማይ እስከ ሚሊንየም አዳራሽ!

  
ከነቢዩ ሲራክ
እኔን ያሰፈራኝ ጎርበጥባጣው መንገድ . . . ኢትዮጵያውያን በግብጽ . . .
ሰሞነኛ የማለዳ ወጌን ወደ እናንተ ላደርስ አንዱን አንስቼ አንዱን ስጥል አንድ ወዳጀ ስልክ ደውሎ በግብጵ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን የአባይን ግድብ ውዝግብ ተከትሎ አደጋ ላይ መሆናቸውን መረጃ ቢጤ አቀበለኝ ። በማስከተልም ከጥቆማ መረጃው ጋር በቀጣዩ ቀን ነዋሪዎች በነቂስ ሰላማዊ ስልፍ ለማደረግ እንዳቀዱ በመግለጽ እንዳነጋግራቸው መከረኝ ። መረጃ ለመሰብሰብ የሚረዱኝን ወንድሞች አድራሻ የሰጠኝን ወንድም አመስግኜ ወደ ሃገረ ግብጽ ካይሮ ደጋግሜ ደወልኩ። ከብዙ ጥረት በኋላ ግን የፈለግኩትን መረጃ ሙሉ በሙሉ ባላገኝም ያገኘሁትን ሰባስቤ ለተጨማሪ መረጃ የሚረዱኝን ተጨማሪ ስልክ ቁጥሮች ሰባሰብኩ። ያሰባሰብኳቸው መረጃዎች ግን ለኢትዮጵያ መጻኤ ህይወት እንድሰጋ እንድፈራ አድርገውኛልና ፈራሁ! ልቤ እንቢ እያለኝ ጥረቴን ገፋሁበት . . . ” በእንቅርት ላይ ጀሮ ደግፍ ” እንዲሉ ድሮም በመገለል ቋፍ ላይ የነበሩት ግብጵ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ስደተኞች የአባይን ግድብ የመንግስታቱ ፍጥጫ ኑሯቸውን እንዳላስመቸው ሰምቻለሁ፣ ደረሰባቸው የተባለው መገለልና ያላባራውን ተደጋጋሚ ጥቃት ለሚመለከታቸው የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ሃላፊዎች “አቤት!” ለማለት የኦነግን እና የግብጽን ባንዴራ ይዘው የተቃውሞ ሰልፍ የማድረጋቸው ዜና ተከታትሎ ደረሰኝ ፣ ይህን መስማቱ በራሱ ያማል . . . እናም ፈራሁ !
ሰላማዊው የሙስሊም ወገኖች ተቃውሞ . . .
ሙስሊም ወገኖቻችን አመት ከመንፈቅ የደፈነ ያልተፈታ ጥያቄ አላቸው ፣ መሪዎቻቸው ዘብጥያ ከወረዱ አመት ከመንፈቅ ሊደፍን ነው ፣ ከዚያም ወዲህ በርካታ ደጋፊዎቻቸው ነጋ ጠባ ዘብጠያ እንደሚወረወሩ እየሰማን ነው ፣ ከሁሉም አስገራሚ በሆነ መንገድ ከአመጽ ርቀው የማህተመ ጋንዲን ሰላማዊ ተቃውሞ ያስናቀ ስላማዊ ተቃውሞ ያሳዩን ሙስሊሞች ለአመት ከመንፈቅ በዋሉት አብዛኛው የአርብ የህብረት ጸሎት በተክታታይ ጊዜያት ” ህገ መንግስት ይከበር ፣ ኮሚቴዎቻችን ይፈቱ!” በማለት ድምጻቸውን ከፍ አድርገው ቢያሰሙም ሰሚ አላገኙም። የታሰሩት የፍርድ ሂደት በገደምዳሜ ሲንከባለል ፣ ሰው ትዕግስቱን እንዳያጣ ያስፈራል። ይህ ሂደትም ውሎ ሲያድ ነገሩ እንዳያከረው ፣ ሰላማዊውን ተቃውሞ በሃይል ሊገታ ከታሰበ ሊፈጠር የሚችለው ሁከት ፣ ሁሉም ሲከር እንዳይበጠስ ፣ ግሎ እንዳይቀልጥ ያሰጋኝ ያስፈራኝ ይዟል ! እናም የመሪ ፣የአስተዳዳሪ፣ የባለ መላ ዳኛ ያለህ አልኩ ቢጨንቀኝ ! ግና ፈራሁ !
ተቆርቋሪ ፣ሳቢ ያጣን ዜጎች በደል …
ይህ ሁሉ ሃሳብ ሲንጠኝ ብዕሬን ወርውሬ ጥዬ ልወጣ ብከጅልም ሌላ ጉድ አዳፍቶ አስቀመጠኝ ። የሰው ክብሩ ቢቀርብን ወደ ውጭ እንደሚላክ እቃ የሻጭ ገዥ ውል መፈጸሚያ ስምምነት ውል በህግ ማዕቀፍ ተላኩ ለሚባሉት ዜጎች አልተበጀልንም። ይህ አያስቆጭ አያንገበግብ ይሆን? ታዲያ ወላጆች ልጆቻቸውን ለገንዘብ ሲሉ ይልካሉ የምንለውስ በየትኛው ሞራል ይሆን? ደላላ ኤጀንሰጀ መውቀሱ ፋይዳው ምኑ ላይ ነው? ከረር ያለው ጥያቄ ማጠየቄ ያለ ነገር አይደለም ። የሰማሁት ቢያመኝ ነው! ዜጋ ከሃገር ለስራ ኮንትራት ሲወጣ ሁለት ሃገራት መካከል ሁለትዮሽ የጋራ ስምምነትና የስራ ውል መሰረታዊ ጥያቄ ነው ። ይህ ግን በእኛ አልሆነም! ለዘመናዊ ባርነት የሚላኩ ዜጎች በደል ከባለቤቶቹ ሌት ተቀን እሰማለሁ ። እናም ጩኸት ምሬቱ ቢታዎሰኝ የሸበበኝ የፍርሃት ልጓም በጥሼ የልብ ልብ የሰጠኝ የነፍስ ውስጥ ሙግት እነሳለሁት ፣ የስደት ቁስሉን የሚያሽረው እውነተኛ መፍትሄ ብቻ ነው በሚል የጀመርኩት የዚያን ሰሞን ጅምር የማለዳ ወግ መልኩን ቀይሬ እንዲህ መሞነጫጨሬን ጀመርኩት ! ያልተደፈሩ ፣ የተደበቁ እውነቶች ቅስማችን እሰከ ሰበረው ስደትና ፍርሃት እዳስሰው ዘንድ አናኳር አንኳር ምክንያቶቸን ደራደርኩ ! ጥቂቶች አስቀድመን የምናውቀውን ፣ ሃላፊዎችን ዳጋግመን ስንጠይቅ “ስምምነት አለ!” ሲሉ ሲወሸክቱን የባጁትን፤የከረሙትን ጭብጥ የሌለው እውነት የጅዳው ቆንስል ጀኔራል አቶ ዘነበ ከበደ ገላልጠው የነገሩን ባሳለፍነው ሳምንት ነበር ። በአብዛኛው በእድሜ ያልበሰሉ ፣ ለዘመነው የአረቦች ቤት አይደለም ፣ ባደጉ በተማሩበት መንደር ዙሪያ ባሉ ወረዳ እና ቀበሌ የዘመኑ ጎጆዎች እንግዳ ለሚሆንባችው ድሃ አደግ ታዳጊ ጉብሎች የሚገኙባቸው ቁጠራቸው ወደ ግማሽ ሚሊዮን የሚጠጉ ዜጎች በኮንትራት ስራ ስም ከዘመናዊ ባርነት ለማይተናነሰው የሳውዲ ባለ ጸጎች የቤት ስራተኝነት ተልከዋል። ይህ የሆነው ግን ያለ ሁለትዮሽ የስራ ኮንትራት ስምምነት መሆኑን የጅዳው ቆንስል አቶ ዘነበ ከበደ ባሳለፍነው እሁድ ከጀርመን ራዲዮ ጋር ባደረጉት ውይይት አርድተውናል ።
በህግና ስርአት ሃገር አስተዳድራለሁ፣ ድህነትን ለማጥፋት የማልፈነቅለው ድንጋይ የለም ከሚል መንግስት ሁለት ሶስት ገጽ የማትሞላ የሰራተኛ ህግን ማርቀቅ እንዴት ገደደው? እንደ ቀሩት ሩቅ ምስራቅ ሃገራት ጠንከር ያለ መብት ማሰከበሪያ አንቀጾችን እንኳ ማስቀመጥ ቢገድ እን ጎረቤት ኬንያ ደመወዝ ፣ የስራ ሰአት፣ ህክምናና መብት ረገጣና የሚከላከሉ ስስ አንቀጾችን አካቶ ፣ ውል ስምምነት ፈጽሞ ዜጎችን በኮንትራት ስራ መላክ ከገደደው መንግስትነቱ ምኑ ላይ ነው? ብየ አጠየቅኩ ፣ ግን መልስ አጣሁ ! ይህም እንዝህላልነት አይሉት ሃገር ማለት ሰው መሆኑን ያለማገናዘብ እዳ? የምናገረው፤ የምለውን ቢያሳጣኝ ፣አንገብግቦ አስቆጨኝ ! የረጅሙ አውራ መንገድ መነሻ መንገድ ማጣት ግራ ያጋባል። ለሃገር ለወገን የሚል መጥፋቱን ማስተዋሌ አራደኝ ! ፈራሁ !
የሰቆቃ እንባ በሚሊንየሙ አዳራሽ . . .
ባለፍነው ሳምንት “በስደት ይብቃ! ” መሪ ቃል ሃገር አቀፍ ስብሰባ በሚሊኒየም አዳራሽ ተካሂዶ ትረሱታላችሁ አልልም ። ዝግጅቱ እንደ ጅማሬው ባይዘልቅም ቀልብን ሳቢ ነበር ለማለት እደፍራለሁ ። የተሰበሰቡት ከፍተኛ የመንግስት ባለስልጣናት እንባና የኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ቀጥታ ስርጭት አስደምሞኛል። ከማውቀው ከሰማሁት ሳይሆን ካየሁት ተነስቼ “ህግን ተከተሉ ይሉናል ! ” እነሱ ግን ህግን አይከተሉም ስል በመረጃ እያስረገጥኩ አጫውታችኋለሁ ብልም ወኔው ከዳኝ. . . እኛ ኢትዮጵያውያን ለሃገራችን ቀናኢ ነን ፣ አሁን አሁን ግን ለሃገሬው ሰው መብት ነጻነት መከበር ብዙም ግድ አለን ብዬ አፊን ሞልቸ ለመናገር ሞራል የለኝም ! ለሰው ልጅ ደህንነት፣ ሰላምና ብልጽግና ቀርቶ ለሰብአዊ መብቱ መከበር ስንተጋ አለመስተዋሉ እየተለመደ ሄዷል ! ግን እኮ ሐገር፤ ምድር ማለት ሰው እኮ ነው ! ሃገሬውን ሰው በዘር በሃይማኖት ሳንለይ ሰብዕናውን ካላከበርነው ካልጠበቅነው ሃገር ያለሰው ምድረ በዳ ነው፣ ሃገር ያለ ሰው ፣ ሰው ያለ ሃገር ምን ትርጉም አለው? ! ብየ ስጠይቅ ችግሩን አወሳስበው እዚህ ያደረሱት ከፍተኛ የመንግስት ሃላፊዎቻችን ለትክክለኛ መፍትሔ የመትጋት ተሞክሮ አሰጋኝና ይህም አስፈራኝ ! አዎ ፈራሁ !
የወገን የሰቆቃ ጥሪ . . .

የአረብ ሃገሩን ስደት እንደ ጋዜጠኛ ወደ ውስጥ ገባ ብሎ ለሚያውቅ እንደኔ ላለ ብኩን ብዙ ለማለት የሚያስችሉ ጥቂት የተጨበጡ ማስረጃዎችን ብቻ ማቅረብ ረዥሙን ውጣ ውረድ በአጭር መቃኘት አይገደውም። ሆኖም ግን መረጃ ማስረጃዎችን በቅርብ ጎላጉሎ ለማሳየት አቅሙ እያለኝ አቅሙ ከዳኝ! እውነቱን ልቦናየ ሲያውቀው” ነገር አብርድ !”የምትለው የአንድ ወዳጀ ይትበሃል በውስጤ ተሰንቅራ አወከችኝ! ይህም ነፍሴ ብዙ ከማለት ገታችኝ ፣ የሁለት ብላቴናዎች አባት ናፍቆት ሲፈትነኝ ፣የፈጣሪ ቸርነት ሰመረ የምለው ህይወቴ ውጤት በእናቷ ሆድ ያለችው” ማህሌት”ለማየት ያለኝ ጉጉት ብዕሬን አነጠፈው! የምወዳት እናቴን ሃገር ቤት ተመልሶ ” የማየት ምኞት መጨናጎል ሲያቆስለኝ “ሃገሬን፤ አፈሬን ዳግም እንዳልረግጥ እሆናለሁ !”የሚለው እኩይ ስጋት ነፍሴን አርቆ አንገላታኝ ! የፍርሃቴ የስጋቴ ደረቅ እውነቱ ይህ ሆነና ሳልፈራው የኖርኩት አስፈሪው ፍርሃት ሳላስበው ጠለፈኝ ! እናም ዝም አልኩ. . .እውነቱን ውሸት ባልልም ላፍታም ቢሆን አፊን በፍርሃት ለጎምኩ ! የወገኔን መከራ፤ ስቃይ ሃገር በግላጭ ፣ መንግስት በድፍረት የተመለከቱትና የአለቀሱት፤ ያነቡት በቁጭት ሲደብኑ አየሁ ! የአስከፊውን ስደት የጉብል እህቶች ስቅየት በውስጤ ያደረውን የተጫነኝን የፍርሃት መንፈስ አሽቀንጥሮ ጣለልኝ ፣ አባረረልኝም ! ተመስገን አምላኬ! የሆድ የሆዴን እነግራችኋለሁ ! እስከዚያው ቸር ያሰማን !
ነቢዩ ሲራክ

No comments:

Post a Comment