Friday, May 3, 2013

የጐንደር ዩኒቨርሲቲ የሕክምና ተማሪዋ ድንገተኛ ሞት እያነጋገረ ነው

    

- አስከሬኑ አጠገብ መርዛማ ነገሮች ከመገኘታቸው ውጭ የታወቀ ነገር የለም
ላለፉት ሁለት ዓመታት በጐንደር ዩኒቨርሲቲ የሕክምና ፋኩልቲ የሕክምና ትምህርቷን በመከታተል ላይ የነበረችው ተማሪ ፀደንያ አስፋው ሚያዝያ 19 ቀን 2005 ዓ.ም. ክራውን በሚባል ፔኒሲዮን ውስጥ ሞታ መገኘቷ እያነጋገረ ነው፡፡
ተማሪዋ ወደ ሦስተኛ ዓመት የሚያሸጋግራትን የፈተና ውጤት ሚያዝያ 18 ቀን 2005 ዓ.ም. ከተመለከተች በኋላ፣ ከዩኒቨርሲቲው ቅጥር ግቢ ወጥታ ባለመመለሷ ጓደኞቿ ሞባይል ስልኳ ላይ ሲደውሉ ምላሽ በማጣታቸው፣ ለፖሊስና ለዩኒቨርሲቲው በማሳወቅ በተደረገ ፍለጋ፣ በማግስቱ ሚያዝያ 19 ቀን 2005 ዓ.ም. ከዩኒቨርሲቲው ራቅ ብሎ በሚገኘው ፔኒሲዮን ውስጥ ሞታ መገኘቷን ጓደኞቿ ገልጸዋል፡፡
በየሆቴሎቹ በተደረገ ፍተሻ ልትገኝ ያልቻለችው ተማሪ ፀደንያ ክራውን ፔኒሲዮን አልጋ የሚይዙ እንግዶችን ስም ዝርዝር ሳያስተላልፍ በመቅረቱ በተደረገ ፍተሻ እዚያ ልትገኝ ችላለች፡፡ ፔኒሲዮኑ የአዳሪዎችን ስም ዝርዝር ለፖሊስ ያላስተላለፈበት ምክንያት ደግሞ፣ አንዲት እንግዳ ዕቃዋን አስቀምጣ ስትመለስ ፎርም እንደምትሞላ ለሪሲፕሽኒስቱ ነግራው በመሄዷና ሳትመለስ በመቅረቷ መሆኑን መግለጹን ተማሪዎቹ ገልጸዋል፡፡ በመሆኑም ከውስጥ በኩል የተቆለፈው ክፍል ሲንኳኳ ሊከፈት ባለመቻሉ፣ ፖሊስ በሆቴሉ ማስተር ቁልፍ ሲከፍተው ሞታ መገኘቷን ጓደኞቿ አስታውቀዋል፡፡
ተማሪዋ ሕይወቷ ጠፍቶ በተገኘበት ክፍል ውስጥ ሁለት መርዛማ የሚመስሉ የመድኃኒት መያዣዎችና ማስታጠቢያ መገኘቱን የገለጹት ጓደኞቿ፣ ምናልባት ልጅቷ የተበላሸባትን የፈጠና ውጤት በማየቷ፣ ራሷን ሳታጠፋ እንዳልቀረች ጥርጣሬ ውስጥ መግባታቸውን አስረድተዋል፡፡
በጣም ጐበዝ ተማሪ እንደነበረችና ፀባይዋም ጥሩ እንደነበር የሚገልጹት ጓደኞቿ፣ ውጤት ተበላሸብኝ በሚል ምክንያት ሕይወቷን የምታጠፋ ልጅ አለመሆኗን በግምት ከመናገር በፊት የሕክምና የምርመራ ውጤት መጠበቅ አስፈላጊ መሆኑን ተናግረዋል፡፡
በተለይ ሞታ የተገኘችበት ክፍል ከውስጥ የተቆለፈና ቁልፉም ተንጠልጥሎ መገኘቱ፣ እንዲሁም ከውጭ በሌላ ቁልፍ ሲከፈት ያለምንም ችግር መከፈቱ “ራሷን በራሷ አጥፍታለች” የሚለውን ግምት የማያስተማምን ስለሚያደርገው፣ የአስከሬን ምርመራ ውጤቱን መጠበቅ ጥርጣሬውን በተወሰነ መንገድ ሊያሻሽለው እንደሚችል ገልጸዋል፡፡
ሟቿ የ21 ዓመት ወጣት መሆኗን የሚናገሩት ጓደኞቿ፣ ለሕክምና ተማሪዎች ፈተና የሚሰጠው ከመቐለ፣ ከጅማና ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲዎች በተውጣጡ መምህራን መሆኑን ጠቁመዋል፡፡ በመሆኑም ሟች ፈተና በወሰደችበት ዕለት አንዱ የውጭ ፈታኝ ከውጤቷ ጋር የተያያዘ ነገር ተናግሯት እንደነበር፣ ይህንንም ከፈተና ስትወጣ ለጓደኞቿ ነግራቸው እንደነበር በዩኒቨርሲቲውና በአካባቢው እየተወራ መሆኑን ተማሪዎቹ ገልጸዋል፡፡ የተበላሸባት ውጤት ምናልባትም ከዚያ ጋር የተያያዘ ሳይሆን እንደማይቀርና ለሕይወቷ ማለፍም ምክንያት ሊሆን ይችላል የሚል ግምት እንዳለ አውስተዋል፡፡
በጐንደር ዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች ተረጋግተው እንዳይማሩ የሚያደርጉ በርካታ የውስጥና የውጭ ችግሮች እንዳሉ የሚናገሩት ተማሪዎቹ፣ ከውጤት ጋር በተያያዘ ተማሪዎች የሚደርስባቸው ማስፈራራት፣ ፈተና እንደሚከብድ በማሳወቅ የሥነ ልቦና ችግር እንዲገጥማቸው ከማድረጉም በተጨማሪ፣ ተስፋ በመቁረጥ አቋርጠው እንዲወጡ የሚደረግበት ሁኔታ ከጊዜ ወደጊዜ እየተባባሰ መምጣቱን ይናገራሉ፡፡
ፆታዊ ትንኮሳና ከውጤት ጋር በተገናኘ የማስፈራራቱ ሁኔታ ግን በከፍተኛ ሁኔታ እየጨመረ በመሆኑ ጉዳዩ በዋናነት የሚመለከተው ትምህርት ሚኒስቴር፣ እንዲሁም መንግሥት ትኩረት ሰጥተው የሚስተካከልበትን ሁኔታ እንዲያመቻቹ ተማሪዎቹ ጠይቀዋል፡፡
በጐንደር ዩኒቨርሲቲ የሁለተኛ ዓመት የሕክምና ተማሪ የነበረችውን ተማሪ ፀደንያ አስፋውን ድንገተኛ ሞት አስመልክቶ፣ ጐንደር ዩኒቨርሲቲ ማብራርያ እንዲሰጥ አሜሪካ የሄዱትን ፕሮፌሰር መንገሻ አድማሱን ተክተው በኃላፊነት እየሠሩ የሚገኙትን ዶ/ር ደሳለኝ መንገሻን በስልክ አግኝተናቸው ማንነታችንን ከገለጽንላቸው በኋላ “ተሳስታችኋል” በማለት ስልካቸውን በመዝጋታቸው፣ አስተያየታቸውን ማካተት አልቻልንም፡፡ አንድ ስማቸው እንዲገለጽ ያልፈለጉ የሕክምና ተቋሙ መምህር እንደሚሉት፣ የልጅቷ አሟሟትና የዩኒቨርሲቲው ተማሪ መሆኗ ግንኙነት የላቸውም፡፡
‹‹ተማሪዋ ሕይወቷ ማለፉ የዩኒቨርሲቲውን ማኅበረሰብ አሳዝኗል፡፡ በዩኒቨርስቲው ውስጥም ሆነ ከዩኒቨርሲቲው ውጭ ብዙ ነገር ሲባል ይሰማል፡፡ ግን ከእውነታው ይልቅ አሉታው ይበዛል፡፡ ተማሪዎች ግቢውን ጥለው ወጥተዋል ይባላል፡፡ ተማሪዎቹ ግን አሉ፡፡ ለቀብር ተከትለው አዲስ አበባ ከሄዱት የተወሰኑት በስተቀር ሁሉም ተማሪዎች አሉ፡፡ ነገር ግን በጣም ተረብሸዋል፡፡ በመሆኑም ሚያዝያ 22 ቀን 2005 ዓ.ም. ከሁሉም መምህራንና ተማሪዎች ጋር አሉ በተባሉ ችግሮች ዙርያ ውይይት ተደርጎ መስተካከል ያለበት እንዲስተካከል፣ መወገድ ያለበት አላስፈላጊ ድርጊት እንዲወገድ ስምምነት ላይ ተደርሷል፤›› በማለት መምህሩ አብራርተዋል፡፡
ከውጭ የመጡ ፈታኝ መምህራን በተናገሯት ነገር ተከፍታ ነበርና ከውጤቱም ጋር በተያያዘ ስለሚወራው ጉዳይ፣ ዩኒቨርሲቲው እያጣራ መሆኑንና እውነት ሆኖ ከተገኘም ዕርምጃ እንደሚወሰድ መምህሩ አስታውቀዋል፡፡ ሚያዝያ 18 ቀን 2005 ዓ.ም. ጠፍታ ሚያዝያ 19 ቀን 2005 ዓ.ም. ሞታ የተገኘችው የፀደንያ አስፋው አስከሬን፣ በዩንቨርሲቲው ተሽከርካሪ ከፖሊስ ጋር ወደ አዲስ አበባ ዳግማዊ ምኒልክ ሆስፒታል ተልኮ፣ አስከሬኑ ከተመረመረ በኋላ ሚያዝያ 20 ቀን 2005 ዓ.ም. ቤተሰቦቿ በሚኖሩበት በኮልፌ ቀራኒዮ ክፍለ ከተማ ዘነበወርቅ መሐንዲስ ሠፈር በሚገኘው ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን የቀብር ሥርዓቷ መፈጸሙ ታውቋል፡፡

No comments:

Post a Comment