Friday, January 3, 2014

በናታችሁ ከዚች አገር አውጡኝ!


Alex Abreham (Facebook)
በናታችሁ ከዚች አገር አውጡኝ ! በቃ ሱማሌም ኧረ ምናምን ሱዳንም ይሁን ብቻ ኢትዮጲያ የምትባል አገር የማልሰማበት አገር ውሰዱኝ !
አሁን ቤት አከራየ መጣና የቤት ኪራይ አምስት መቶ ብር ጨምር ሲለኝ ቤት አከራየ ሳይሆን ኢትዮጲያ አስጠላችኝ !! የቤት ኪራዩ ብቻ እንዳይመስላችሁ የግፍ አገር ናት ! ምንም ፍትሃዊ ነገር የላትም ! እንደድመት ወልዳ የምትበላ ጉድ !
እስካሁን የኖርኩበትን እድሜ ቢያንስ ሶስት አራተኛውን አንገቴን ደፍቸ በመማር አሳልፊያለሁ በተማርኩት ሙያም እችን ለዛዋ የተሟጠጠ አገር አገልግያለሁ ! በምሰራው ስራ በመስሪያ ቤቴ የተመሰገንኩ ባለሙያ ነኝ ! ግን አንድ ቀበሌ ለቀበሌ እያውደለደለ በአፉ የሚኖር መሃይም የቤት ባለቤት አፉን ሞልቶ ወይ ልቀቅ ወይ አምስት መቶ ብር ኪራይ ጨምር ይለኛል! የዛሬ አራት ወር ሁለት መቶ ብር አስጨምሮኛል እውነቴን ነው በአገሬ ላይ የማልጠቅም ዜጋ የመሆን ስሜት ነው የተሰማኝ ፡፡
እኔ ማንም ብር እንዲሰጠኝ አልፈልግም ሰርቸ ማግኘት የምችል ጤነኛ የተማርኩ ወጣት በመንግስት ችግር ምክንያት እንደለማኝ መመፅወት አለብኝ እንዴ እንደገና ለፍተው ያሳደጉ ቤተሰቦቸ ለእኔ ብር መደጎም አለባቸው እንዴ እንደህፃን ልጅ ለኔ ልብስ መግዛት አለባቸው እንዴ…. ውለታየን መክፈል ቢያቅተኝ እንኳን እንዳልችል እንዴት በማንም ሆዳም እገፋለሁ መብቴን እቀማለሁ
አንድ የሱማሌ ወይም የኤርትራ ስደተኛ ከእኔ የተሸለ እኔ አገር ላይ ይኖራል ! እንደዜጋ መብራት ውሃ በስርአት አላገኝም ያውም ከፍተኛ የሚባል የስራ ግብር እየከፈልኩ ! እንደዜጋ ትክክለኛ መረጃ አላገኝም ! እንደዜጋ ደፍሬ ስለችግሬ አላወራም ! ላቤን ጠብ አድርጌ የምኖር ዜጋ አባትና እናቴ እድሚያቸውን ሙሉ በፍፁም ታማኝነትና ትጋት ያገለገሏት ኢትዮጲያ ላይ እንደሁለተኛ ዜጋ መንከራተት እጣ ፋንታየ ሁኗል …… ኧረ የምን ሁለተኛ ምንም ደረጃ የሌለኝ ውዳቂ ዜጋ ነኝ እንጅ ! በእውነት ግን እኔ ትላንት ዩኒቨርስቲ ሁኘ ኢትዮጲያን የብርሃን ኩሬ አድርጌ ሳልም የነበርኩት ልጅ ነኝ …..ኦህህህ እውነቴን ነው እንደዛሬ መሮኝ አያውቅም !
ከአቅሜ በላይ እየሰራሁ የለፋሁበት ደመወዝ አምስት ሳንቲም ለመንግስት ግብር በማይከፍል ቤት አከራይ ሲቀማ መንግስት አድገሃል ልማት ምናምን እያለ ይቀባጥራል ! ወጣት ነኝ ጥሩ መልበስ ጥሩ መመገብ አለብኝ ለፍቸ ያገኘሁትን ብር በስርአት ልጠቀምበት መብት አለኝ …. በተዘዋዋሪ የመንግስት ስንፍና እና ሃላፊነቱን አለመወጣት ለማንም ስግብግብ መጫወቻ እያደረገን ነው !
የዛሬ አርባ አመት እች አገር እዛ ትድረስ እዚህ ስሜት አይሰጠኝም ወጣትነቴን እንደቀልድ በባዶ ተስፋ የምትበላ አገር ለኔ ምኔ ናት ጠልቻታለሁ አገሬን !! በውጭ አገር የሚኖሩ እንዴት የታደሉ ናቸው ! እየሸሹ ባህር የበላቸው ከፎቅ የተወረወሩ ምንኛ እድለኛ ናቸው !
ኢትዮጲያ ተስፋችንን የምታኮስስ ተስፋ ቢስ አገር ናት !! እንደዜጋ በደልን ድህነትን ፍርሃትና መሸማቀቅን ብቻ የምታሸክም አገር ናት አገሬ ! ሽ አመት በባርነት መኖር ይሻላል ኢትዮጲያ ውስጥ ከመኖር ! ስንት ጊዜ ችግሯን እንዳላየን በእናትነት ሸፋፍነን አለፍናት ስንት አመት ሙሉ ቻልን በባዶ ተስፋ ተምራችሁ ያልፍላችኋል እያሉን ዶክተር ብትሆን ኢንጅነር ምን በትሆን ምን ወፍ የለም ! ሙሰኛ አጭበርባሪ ውሸታም አስመሳይ ስትሆን ከሰውነት ክብርህ ዝቅ ስትል ብቻ እንደለማኝ ፍርፋሪ ትወረውርልሃለች !
አገሬን ጠልቻታለሁ ! ሰርቸ ለምኖር ለፍቸ ለምኖር ለእኔ ኢትዮጲያ ያደረገችልኝ ነገር ቢኖር የለፋሁበትን ገንዘብ በስግብግብነት መቀማት ብቻ ነው ! እግዚአብሄር እዚች አገር ላይ የፈጠረኝ ለምንድን ነው ? ማንም ሰው ከዚህ አስቀያሚና የግፍ የበደል የአድሎ አገር ቢያስወጣኝ እግሩ ላይ ወድቄ ከመሳም አልመለስም ! አገሬን ጠልቻታላሁ ! መልስ የሚሰጥ የሚጨነቅልኝ መንግስት የለኝም !! አገሬ ዛሬ በውስጤ ሙታለች !

በቅሎና ፈረሰ እኩል ፈሰስ


ታደለ መኩሪያ
አቶ ዳኛቸው ቢያድግልኝ፤ ‘ልጓም የበጠሰው የፕሮፌሰር መስፍን ወልደ ማርያም የስድብ ፈረስ’ በሚል አርዕስት ፕሮፌሰሩ ባቀረቧችው ሁለት ጹሑፎች ላይ ትችታቸውን አቅርበዋል። እነርሱም አበሻና ልመና፤ አበሻና ሆድ ናቸው።Prof. Mesfin Woldemariam : is an Ethiopian Human Rights activist and philosopher
አቶ ዳኛቸው የፕሮፌሰሩን ጽሑፎች መገመገማቻው ወደ ኋላ ተመልሼ አንደንድ የፕሮፌሰሩን ሥራቸው ለመከለስ አስችሎኛል፤ በዚህ አመሰግናቸዋለሁ፤  ከትችት ትምህርት ማግኘትን ግንኙነትንም ለመፍጠር መቻሉን ፕሮፌሰሩ የሚያምኑ መሆናቸውን ከአንዳንድ ጹሑፋቸው ለመረዳት ችያለሁ፤ ስለሥራቸው እንጂ ስለግድላቸው አላትትም፤ የአቶ ዳኛቸው ሐሣብ የራሳቸው መሆኑን እቀበላለሁ፤ ግን የሣቱትን  በማስረጃ ለማሳየተ እሞክራለሁ፤ ጉዳዩ ስለ አቶ ዳኛቸው ወይም ስለፕሮፌሰሩ አይደለም ሁላችንንም ስለሚመለከተን የጋራ ችግር ነው።
እላይ ከቀረቡት  አበሻና ልመና፤ አበሻና ሆድ ከሚሉት ውስጥ ትኩረት የሰጧቸውን ከማቅረቤ በፊተ ለግንዛቤ  አቶ ዳኛቸው ቢያድግልኝ ለትችታቸው መደርደሪያ ያቀረቡት አረፍተነገር እነሆ፤ ‘ይህ ዕውቀትንና ሁኔታን ያላገናዘበ መፍትሄ የመጠቆም ፣ የማስተማር አቅምም የሌለው፣ ኢትዮጵያዊነትን የሚያዋርድ፤ ጅምላስድብን ሽሙጥ በተከታታይ ሲወርድብን አይቶ እንዳላየ ማለፍ ክብራችንንለማግዶፍናለማዋረድኢትዮጵያችንንለማቋሸሽለሚተጉ ዱላ ማቀበል ይሆናል። ጸሐፊ እዚህ ላይ ሚናቸውን  አለዩም ዱላ እያቀበሉ ያሉት፤ ክብራችንን ለአቋሽሹት ሀገራችንን ለአዋረዱት በሥልጣን ላይ ላሉት ወያኔዎች ወይስ ለፕሮፌሰር መስፍን ወልደማሪያም? ጅምላስድብ አበሻና ሆድ በሚለው ፡ ‘ሆድ ስላለው ወይም የሚበላው ስላለው አበሻ ነው’ ብለው በግልጽ አስቀምጠውታል፤ በጅምላ አይደለም ለማለት ነው። አእምሮውን ተጠቅሞ ከሆዱ በላይ ነፃነቱን ስለሚጠይቀው ስው ያለመሆኑን የሚጠቁም ነው። ይህን በምን አወከው? እመለሰበታለሁ። አቶ ዳኛቸው ከፕሮፌሰሩ ጹሑፎች ጨምቀው ያወጧቸውን እንይ፤ ‘በዓለም ሕዝቦች መሀከል ውድድር ቢደረግ ያለጥርጥር አበሻ አንደኛ ከሚወጣባቸው ነገሮች አንዱ ልመና ሳይሆን አይቀርም፣ ለአበሻ ልመና የኑሮ ዘዴ ነው’
ፕሮፌሰር መስፍን ወልደ ማርያም ከዚያ ድምዳሜ ላይ መድረሳቸው ነው አቶ ዳኛቸውን ያስቆጣቸው የሚመስለው፤ ድምዳሜ ላይ የደረሱትም ከግብተኝነት እንጂ በጥናት ላይ ያልተመሰረተ ክብራችንን ለማቋሸሽ ሆን ብሎ እንዳቀረቡት ለማመልከት ሞክረዋል።
መክሸፍ እንደኢትዮጵያ ታሪክ መስፍን ወልደማሪያም 2005 ዓ ም ከገጽ 194_195 ውስጥ እውነትን የመፈለጊያ ዘዴውን አስቀምጠውልናል። የተረጋገጠ እውነት ሊገኝ የሚችለው በዕውቀት ሲሆን ሌላው እውነት ከእምነት እንደሆነ ነው። ኢትዮጵያ የሃይማኖት ሀገር ሰለሆነች የእኛ እውነት የሚመነጨው ከእምነት ነው ማለት ነው። ለምርምር ለክርክር ክፍት አይደለም። ከዕውቀት የሚነሳው ደግሞ የተረጋገጠ እውነት ነው። ለምርምር ለጥያቄና ለክርክር ክፍት ነው።ፕሮፌሰሩ ያለጥርጥር አበሻው አንደኛ ከሚወጣባቸው ነገሮች አንዱ ልመና ሲሉ፤ ዕውቀቱን  በተረጋገጠ እውነት ላይ መሠረቱን አድርጉ ሀብተ ሰቡን፣ ሀብተ ምድሩን ተጠቅሞ ያለማደጉንና በልመና መኖሩን ለማመላከት ነው። የዕውቀት ጉዳናን እንዳይከተል በሃይማኖት ብቻ በሚገኝ እውነት መሠረት አድርጎ ልመናን የኑሮው ዘዴ ለማድረጉ ምክንያቶችን አቅርበዋል።
‘ብልጦች እግዚአብሔርን የሚለምኑት ሥልጣን፣ ሐብትና ጉልበት ነው።እግዚአብሔር ፍርዱን እስኪሰጥ ድረስ የተለያዩ ስሞችን እየለጠፉ በተዋረድ የለማኞችን ሠራዊት ያደራጃሉ፤ ሕዝብ ሁሉ ከነዚህ የለማኞች ሠራዊት አንዱ ውስጥ ለመግባት በፉክክር ይተላለቃል፤ሠራዊት ውስጥ በመግባት የሚገኘው ጉርሻ ልጆቻቸውን እንኳን ከረሃብ የሚያድን መሆኑን ሳይገነዘቡ መብቻቸውን እያስረገጡ የሌሎችን መብት ለመርገጥ መሣሪያ ይሆናሉ።እነዚህ እንግዲህ ልመናን በማሕበረሰቡ ውስጥ ተክለው እየኮተኮቱ የሚያስፋፉ ናቸው፤ልመናን ባህል የሚያደርጉት እነዚህ ናቸው።’ በነገራችን ላይ ፕሮፌሰር መስፈን ወልደማሪያም የታወቁ ለማኝ ናቸው፤ 1950 አካባቢ የትግራይ ሕዝብ ተርቦ በግላቸው የሸዋ ገበሬዎችን ለምነው ለተራበው ሕዝብ አድረሰዋል፤ በ1966 ዓ ም ስለረሃብ አስከፊነት ለሕዝብ ሲያሰሙ በመንግሥት ታስረዋል፤ የኢትዮጵያው ዮሴፍ የሚል የቅጽል ስም አሰጥቷቸዋል።
‘አዳም አበሻ ሳይሆን አይቀርም ሁሉንም ነገር ብላ ከተባለው በቀር ብሎ ያስቀመጠው ይመስላል ፤ በላባችሁ ወዝ ብሉ ተብለው አዳምና ሔዋን መረገማቸውን አበሻ ገና አልሰማም አበሻ የተፈጠረው ገነት ውስጥ ቁጭ ብለህ ያለውን ሁሉ ብላ በተባለበት ጊዜ ነው፤እግዚአብሔር አበሻን ሁሉንም ብላ ሲለው ምንአልባት በጆሮው ጭራሽ አታስብ ብሎት ይሆናል።’  ነፃ ተፈጥሮው የፈጣሪውን ትዕዛዝ እንኳን እስከመጣስ  ያደርሰዋል ግን የአበሻው አዳም ይህ ለምን ተሳነው ነው የፕሮፌሰሩ ጥያቄ፤ የሰራው ሁሉ እየተባረከለት ለሚኖርባት ፣ረሃብ፣ችጋርና በሽታ የሚባል ነገር ከማይታወቅባት ገነት ወይም ጄነት ከተባለች ሥፍራ ወደ አደገኛይቱና በውስጧም ያሉ ፍጥረታት ሁሉ በጥረቱ ካላሸነፈቸው በስተቀር ሊጎዱት ወደሚችሉባት ምድር መጣሉን የሃይማኖት ሰባኪዎች ይሰብካሉ፤ ሆኖም ፈጣሪው ሰውን ወደ ምድር ሲወረውረው ከነፃነቱ ጋር መሆኑን አይሰብኩም። አዳም ያላደረገውን እኛ ኢትዮጵያዊያን ነፃነታችን  አስገፍፈን ለሆዳችን ማደራችን ስለአዳም የተነገረው አልገባንም ወይም በተሳሳተ ሁኔታ ወስደነዋል ማለት ነው። አዳም ነፃነቱን ባይሻ ኖሮ በገነት የቀረበለትን አየበላ ሆዱን እየሞላ ይኖር ነበር። ግን የማወቅ ነፃነቱን ፈለገ፣ ከሆድ ነፃነትን መረጠ፤ለዚህም ዋጋ ከፈለ፤ ከገነት ወይም ጄነት ተባረረ፤ በምድር ሰው በሰው ጭቆናን ለመቋቋም ብዙዎች ሕይወታቸውን ሰጥተዋል፤ በሀገራችንም ለነፃነታቸው ብዙዎች በእስር በግድያ እየተሰቃዩ ይገኛሉ፤ ፕሮፌሰሩ በመግቢያቸው እንደጠቀሱት ሆድ ሰላለው ወይም ሰለሚበላው አበሻ ነው ትንታኔ ያቀረቡት በአጭሩ ሕግ አዳምን ጥሶ ለሆዱ ያደረ ማለታቸው ነው። ለነፃነታችን ካልቆምን እኛንም ይጨምራል። በነፃነት፣ በፍትሕ፣ ሕግ አስከብረን እየኖርን ቢሆን ሆዳምነት ስድብ አይሆንም ነበር። አቶ ዳኛቸው ከነጮቹ በላይ ሆነን ነው ወይ የምንሰደበው ብለው በቁጭት ሐሣባቸውን ገልጸዋል፤ አሁን አሳቡ የገባቸው ይመስለኛል።
ከአቶ ዳኛቸው ቢያድግልኝ ጋር አንድ የምጋራቸው ሐሣብ አለኝ፤ ፕሮፌሰር መስፍን ወልደ ማሪያም የሚታወቁት ከንጉሡ ጀምሩ በአስተዳደሩ ላይ ቅዋሜ በማሰማት መፍትሄም በማቅረብ  ነበር።መሪዎቹ አልሰማ ማለታቸውን ተረድተው ይመስላል ድርና ማግ ሆነው በመብት ግፈፋው ላይ ከተሰማሩት ስብስቦች ላይ ጹሑፋቸው ያተኩራል፤ ያም ሁኔታ ከወያኔ ጋር እየዘረፉ እያዘረፉ ገለው እያስገደሉ ከሰላማዊ  ሕዝብ ጋር ተቀላቅለው ወያኔ ወያኔ የሚሉትን ነጥሎ ለማውጣት ያነጣጠረ ይመስላል።
የአቶ ዳኛቸው ቢያድግልኝ ወቀሳ መሰል ትችት ከቃላት አመራረጥ የቸግሩን ምንጭ ለማግኘት ያለመጣር ዳተኛነትን ያጸባርቃል።  ብዕራቸው መልክቱ ላይ ሳይሆን መልክተኛው ላይ ያተኮረ ይመስላል። በኦሮሞኛ አንድ ተረት አለ ‘ኡዳን ኪያ ሚኒን ኪያሚቲ’  አይን ምድሩ የኔ ነው የኮሶ ትሉ የኔ አይደለም፤ ይህን ፓራሣይት የኮሶ ትል መራራውን ኮሶ ጠጥቶ ከማስወገድ ይልቅ ኮሶ ማታ በማለት ማባበሉ የኮሶ ትሉን አያስወግደውም።
ታደለ መኩሪያ
tadele@shaw.ca